Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያ ፣ ሱዳን እና ግብፅ በህዳሴ ግድብ ዙሪያ የሚያካሂዱት የሶስትዮሽ ውይይት በነገው ዕለት እንደሚጀምር ተገለፀ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 16፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብፅ በህዳሴ ግድብ ዙሪያ የሚያካሂዱት ውይይት በነገው ዕለት እንደሚጀምር የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበርና የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎሳ አስታወቁ።
 
ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ ከሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሀምዶክ እና ከግብፁ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ ጋር ሰፊ ውይይት ከተካሄደ በኋላ በግድቡ ዙሪያ የሚደረገው ውይይት በነገው ዕለት እንደሚጀመር የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ሲሪል ራማፎሳ መናገራቸውን ከሀገሪቱ መንግስት ድረ ገፅ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
 
ፕሬዚዳንት ራማፎሳ በትብብር መንፈስ፣ በፈቃደኝነት እና በሁሉም ዘንድ ተቀባይነት ያለው ስምምነት ላይ ለመድረስ ሀገራቱ ላሳዩት ተነሳሽነት ምስጋና አቅርበዋል።
 
በአፍሪካ ህብረት ድጋፍ በሚደረገው የሶስትዮሽ ውይይት ሰላማዊ እና ትብብራዊ መፍትሄ ለመስጠት በሶስቱ ሀገራት መሪዎች ዘንድ ጠንካራ ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት እና ተነሻሽነት እንዳለ ፕሬዚዳንቱ ገልፀዋል።
 
ይህም ሶስቱ ሀገራት ለአፍሪካ ህብረት የማዕዘን ድንጋይ ለሆነው ለአፍሪካውያን ችግር አፍሪካዊ መፍትሄ መስጠት ላይ መተማመን እንዳላቸው የሚያሳይ ነው ብለዋል።
 
ፕሬዚዳንቱ ሶስቱ ሀገራት ቴክኒካዊ እና ህጋዊ ጉዳዮችን ጨምሮ በቀሪ ጉዳዮች ስምምነት ላይ ይደርሳሉ የሚል እምነት እንዳላቸውም ነው የገለጹት፡፡
 
የህዳሴ ግድብን በተመለከተ የሚደረስ ስኬታማ ስምምነት ቀጠናዊ ውህደትን እንደሚያፋጥን የገለፁት ፕሬዚዳንቱ ለአፍሪካም ሆነ ለቀጠናው ቀጣይነት ያለው ልማት እና ትብብር ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል።
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.