Fana: At a Speed of Life!

ዊሊያም ሩቶ 5ኛው የኬንያን ፕሬዚዳንት ሆነው ተመረጡ

አዲስ አበባ ፣ ነሐሴ 9 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በኬንያ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዊሊያም ሩቶ አሸነፉ።

ምክትል ፕሬዚዳንቱ ዊሊያም ሩቶ የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር ራይላ ኦዲንጋን በጠባብ ውጤት ማሸነፋቸውን የሀገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ይፋ ያደረገው ውጤት ያመላክታል።

በምርጫው ሩቶ ከ50 በመቶው በላይ ድምጽ አግኝተዋል ነው የተባለው።

ከ14 ሚሊየን በላይ ኬንያውያን ድምጽ የሰጡበት የኬንያ ምርጫ፥ አራት ዕጩዎች ተፎካክረውበታል።

በኬንያ የምርጫ ሕግ መሠረት አንድ ዕጩ ተወዳዳሪ ፕሬዚዳንት ሆኖ ለመመረጥ 50+1 እና ከ47ቱ የሀገሪቱ ክልሎች በ24ቱ ክልሎች ከ25 በመቶ በላይ ድምጽ ማግኘት ይኖርበታል።

በምርጫው ሩቶ 50 ነጥብ 49 በመቶ ድምጽ ሲያገኙ፥ ራይላ ኦዲንጋ ደግሞ 48 ነጥብ 8 በመቶ ድምጽ ማግኘታቸውን የምርጫ ኮሚሽኑ ይፋዊ ውጤት ያመላክታል።

ኬንያ በፕሬዚዳንታዊ የፖለቲካ ሥርዓት የምትመራ ሀገር ስትሆን የመድብለ ፓርቲ የፖለቲካ ሥርዓትን የምትከተል ሀገር እንደሆነች ይነገራል፡፡

ኬንያ ከብሪታንያ ቅኝ ግዛት ነጻ ከወጣች በኋላ በፈረንጆቹ 1963 የኬንያው የአፍሪካ ብሔራዊ ኅብረት (ካኑ) ፓርቲ ሀገሪቷን በራስ-ገዝ አስተዳደር ለመምራት መንበረ-ሥልጣኑን ተረክቧል፡፡

ጆሞ ኬንያታም በዚሁ ዓመት የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት በመሆን ሀገሪቷን እስከ ፈረንጆቹ 1978 ድረስ ኬንያን መርተዋል፡፡

በመቀጠልም ዳንዔል አራፕ ሞይ ሁለተኛው፣ ሙዋዪ ኪባኪ ሦስተኛው እንዲሁም ኡሁሩ ኬንያታ አራተኛው ፕሬዚዳንት በመሆን ኬንያን መርተዋል፡፡

ተመራጩ ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ሀገራቸውን ለ10 አመታት በምክትል ፕሬዚዳንትነት አገልግለዋል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.