Fana: At a Speed of Life!

የህወሓትን ጁንታ ቡድን የሚቃወም ሰልፍ በወላይታ ሶዶ ተካሄደ

አዲስ አበባ ፣ ህዳር 5 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የሀገር አፍራሹን ህወሓት በመቃወምና የኢትዮጵያ መንግስት በሴረኛው ጁንታ ላይ እየወሰደ ያለውን እርምጃ በመደገፍ በወላይታ ዞን ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ።

ከሀገር አልፎ ለአፍሪካ ኩራት በሆነው መከላከያ ሰራዊት ላይ የተደረገው የጀርባ ጥቃት የወላይታን ህዝብ እጅግ ማስቆጣቱን ሰልፈኞች ተናግረዋል።

ይህንኑ አስነዋሪ የስግብግብ ጁንታ ቡድን ድርጊት በመቃወምም በወላይታ ሶዶ ከተማ ከሁሉም የዞን የከተማና የወረዳ መዋቅሮች የተሰባሰቡ የህብረተሰብ ክፍሎች በሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሟቸውን ገልፀዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት በዚህ ስግብግብ ቡድን ላይ እየወሰደ ያለውን እርምጃም በወላይታ ሶዶ ሁለ ገብ ስታዲየም በመሰብሰብ ነው በድጋፍ ሰልፍ የገለጹት።

በሰላማዊ ሰልፉ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ዶክተር እንድሪያስ ጌታ በጀግናው መከላከያ ሠራዊት ላይ የደረሰውን አስከፊና አስነዋሪ ድርጊት በመቃወምና ከመንግሥት ጎን በመቆም ድጋፍ ለማድረግ ለተሰበሰበው ህዝብ ምስጋና አቅርበዋል።

አስተዳዳሪው አክለውም ሕብረተሰቡ ለአካባቢው ሰላምና ፀጥታ ዘብ በመሆን ለሀገር መከላከያ ሠራዊት አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።

አንዳንድ የሰልፉ ታዳሚዎች ለጀግናው መከላከያ ሠራዊት ድጋፍ እንዲሆን የደም ልገሳ አድርገዋል።

በመለሰ ታደለ እና ማቱሳላ ማቴዎስ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.