Fana: At a Speed of Life!

የበጎ ፈቃደኛ የህክምና ባለሙያዎች ቡድን በጥቃት የተጎዱ ዜጎችን ለመርዳት ወደ ቡለን ወረዳ ለመጓዝ ተዘጋጀ

አዲስ አበባ ፣ ታህሳስ 17 ፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ቡለን አካባቢ በተፈጸመ ጥቃት ጉዳት ለደረሰባቸው ዜጎች የህክምና እርዳታ የሚሰጥ የጤና ባለሙያዎች ቡድን ከፓዌ ሆስፒታል ነገ ወደ ስፍራው ለመጓዝ መዘጋጀቱ ተገለጸ፡፡

የክልሉ ጤና ቢሮ እንዳመለከተው በበጎ ፈቃደኝነት ለተደራጀው የህክምና ባለሙያዎች ቡድን ለህክምና እርዳታ የሚያግዝ ግብዓት ተሟልቶለታል።

በመተከል ዞን የቡለን ወረዳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር አቶ ሲሳይ ምስጋና እንዳሉት፤ ሰሞኑን በወረዳው በኩጂን ጨምሮ በተለያዩ ቀበሌዎች በተፈጸመ ጥቃት ብዛት ያላቸው ተጎጂዎች ወደ ሆስፒታሉ መጥተዋል፡፡

በሆስፒታሉ የሚገኙት ተጎጂዎች አፋጣኝ ህክምና ካላገኙ ለከፋ ጉዳት ሊዳረጉ እንደሚችሉም አስረድተዋል፡፡

ሆስፒታሉ 40 የህክምና አልጋዎች ብቻ እንዳሉት ያመለከቱት አቶ ሲሳይ፤ “ያሉት ውስን አልጋዎች አብዛኞቹ በመደበኛ ታካሚዎች ተይዘዋል” ብለዋል፡፡

በሆስፒታሉ የመድሃኒት አቅርቦት፣ አልጋ እና ሌሎችም ግብዓቶች እጥረት በመኖሩ በጥቃቱ ለተጎዱ ወገኖች ተገቢውን ህክምና መስጠት ማዳገቱን ተናግረዋል፡፡

የክልሉ ጤና ቢሮ ሃላፊ አቶ ፈቃዱ ረጋሳ በበኩላቸው በርካታ የጥቃቱ ተጎጂዎች በሚገኙበት በቡለን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል አፋጣኝ ህክምና ለመስጠት ከፓዌ ሆስፒታል በበጎ ፈቃደኝነት የተደራጀ የህክምና ባለሙያዎች ቡድን ወደ ስፍራው ለመጓዝ መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡

“ከህክምና ባለሙያዎቹ ቡድን በተጨማሪ መድሃኒት፣ ቁሳቁስ እና ተያያዥ ግብዓቶች በነገው ዕለት ወደ ቡለን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ይደርሳል” ብለዋል፡፡

በጎ ፈቃደኛ ባለሙያዎቹ እና የህክምና ግብዓቱ የሚጓዙት በሃገር መከላከያ ሠራዊት እጀባ እንደሆነ አቶ ፈቃዱ ማስታወቃቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል www.youtube.com/fanatelevision ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.