Fana: At a Speed of Life!

የብር ኖት ላይ የተደረገው ለውጥ የኢኮኖሚ መዛባትን በማስተካከል ፖለቲካዊ መረጋጋትን ይፈጥራል- የፖለቲካ ፓርቲዎች

አዲስ አበባ፣ መስከረም 8፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያ በቅርቡ ያደረገችው የገንዘብ ኖት ቅያሪ የኢኮኖሚ መዛባትን በማስተካከል ፖለቲካዊ መረጋጋትን ይፈጥራል አሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች።

ከፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ጋር ቆይታ ያደረጉት የኢትዮጵያ ሶሻል ዲሞክራሲ ፓርቲ ሊቀ መንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፣ የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ትብብር ሊቀ መንበር ዶክተር አረጋዊ በርሄ እና አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ ትዕግስቱ አወሉ በጥናት ላይ ተምስርቶ የብር ኖቱ መቀየሩ በህገ ወጥ መንገድ የሚፈፀሙ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ አሻጥሮችን በማስቀረት ሰላም እና መረጋጋት እንዲፈጠር ይረዳል ብለዋል።

የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ትብብር ፓርቲ ሊቀመነበር ዶክተር አረጋዊ ብርሄ፥ ከባንክ ውጪ የሚንቀሳቀሰው ገንዘብ ህጋዊ ያልሆነ የሸቀጥና የገንዘብ ዝውውርን ይፈጥራል ይላሉ።

የገንዝብ ዝውውሩ በሀገር ውስጥ እና በውጪ እየሰፋ በመሄድ ጠብደል ሙሰኞች እየፈጠረ መንግስታዊ ስርዓትንም ፈትኗል ባይ ናቸው።

አሁን መንግስት በገንዘብ ኖት ላይ ያደረገው ለውጥ ከኢኮኖሚው ባሻገር በፖለቲካ ምህዳሩ ላይ ተጽህኖ ይፈጥሩ የነበሩ ሴራዎችን በማስቀረት የተረጋጋ ፖለቲካ እንዲኖር ያድረጋል ነው የሚሉት።

ከባንክ ውጪ የሚዘዋወረው ገንዘብ ከፍተኛ መሆኑ ህጋዊ ስርዓቱን ከማዛባቱም በላይ እንደ ጦር መሳሪያ ያሉ ህገ ወጥ ንግዶች እና ዝውውርን እንዲበራከት ማድረጉን አንስተዋል ዶክተር አረጋዊ።

የኢትዮጵያ ሶሻል ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ሊቀ መንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፥ መንግስት በጥናት ላይ በመመስረት የሚወስዳቸው እርምጃዎች ስላምና መረጋጋት እንዲፈጠር በማድረግ በኩል ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።

መንግስት የገንዘብ ኖትን በመቀየር የወሰደውን እርምጃን ፓርቲያቸው የሚደግፍ እና የሚቀበለው መሆኑንም ተናግረው፤ ሌሎች የደረሰባቸውም ክፍተቶች ጥናት ላይ ተመስርቶ ማሻሻያዎችን እንዲያደርግም ፕሮፎሰር በየነ ጠይቀዋል።

የአንድነት ለፍትህና ዴሞክራሲ ሊቀ መንበር አቶ ትዕግሰቱ አወሉ በበኩላቸው፥ የብሄራዊ ባንክ ያወጣው የጥሬ ገንዘብ እንቅሰቃሴ ገደብ ከብር ኖት ቅያሪ ጋር በጥንቃቄ ተገባራዊ የሚደረግ ከሆነ ለሀገሪቱ የፖለቲካ ሽኩቻ እንደ አንድ መፍትሄ ያገልግላል ብለዋል።

በተለይም በህገ ወጥ መንገድ ተስብስቦ ለህገ ወጥ አላማ የሚውል ገንዘብ በማስቀረትም ህዝቡና ሀገሪቱ ለሚፈልጉት ዘላቂ ሰላም መስረት ይጥላል የሚል እምነት አላቸው።

የብር ኖት ለውጡ እንዲያመጣው የተቀመጣው ግብ እንዲሳካ ግን የብሄራዊ ባንክ የጥሬ ገንዘብ ዝውውርብ ለመቆጣጠር ያወጣውን መመሪያ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ መሆነን ማረጋገጥ አስፈላጊ መሆኑ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮቹ ገልጸዋል።

በበላይ ተስፋዬ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.