Fana: At a Speed of Life!

የህዳሴ ግድብ ግንባታ የተፋሰሱን አገራት የጋራ የተጠቃሚነት የሚያጠናከር ነው- አቶ ገዱ

አዲስ አበባ ፣ ነሃሴ 9፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የተፋሰሱን አገራት ፍትሃዊና የጋራ የተጠቃሚነት የሚያጠናከር መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ገለፁ።
 
“የታላቁ የህዳሴ ግድብ ቁልፍ ጉዳዮች፣ የወደፊት አገራዊ አቅጣጫና የዳያስፖራው ሚና” በሚል ርእስ በበይነ መረብ ውይይት ተካሂዷል።
 
በውይይቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ጨምሮ በናይል ተፋሰስ አገራት የሚገኙ የኢፌዲሪ አምባሳደሮች ተሳትፈዋል።
 
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚኖሩ መላ ኢትዮጵያዊያን በራሳቸው ወጪ የሚገነቡት ፕሮጀክት በመሆኑ የመጀመሪያ ዓመት ዉሃ ሙሊት በተሳካ ሁኔታ በመከናወኑ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል አቶ ገዱ።
 
ኢትዮጵያ ያላትን የውሃ ሀብት መጠቀም የሀገሪቱን ህልውና ልማት የማስጠበቅ ጉዳይ መሆኑንም አብራርተዋል።
 
በአፍሪካ ህብረት ማዕቀፍ በደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎሳ ሰብሳቢነት በሶስቱ አገራት መካከል የሚካሄደው ድርድር አበረታች ውጤት የታየበት መሆኑንም አንስተዋል።
 
የናይል ተፋሰስ አገራትን የጋራ ተጠቃሚነት ለማሳካት የሚያስችለው የናይል ትብብር ማዕቀፍን ለመመስረት በአባል አገራቱ የተጀመረውን የትብብር ማዕቀፉን የማጽደቅ ሂደት በማጠናቀቅ ወደ ተግባር ማስገባት ወሳኝ መሆኑንም አቶ ገዱ ገልጸዋል።
 
ሁሉም ኢትዮጰያዊያ ግድቡ እስኪጠናቀቅ ድረስ እስከዛሬ እያደረገ ያለውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል አምባሳደሮቹ የሚያደርጉትን ጥረት አጠናክረው እንዲቀጥሉም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጥሪ ማቅረባቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ፅህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
 
መላ ኢትዮጵያዊያን በአገራዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት እንዲኖራቸውና የጋራ አቋም ለመያዝ መሰል መድረኮች ወሳኝ በመሆናቸው መጠናከር እንዳለባቸው በማሳሰብ የመድረኩን አዘጋጆችን አመስግነዋል።
 
በውይይቱ በናይል ተፋሰስ አገራት የሚገኙ የኢፌዲሪ አምባሳደሮችና በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ተደራዳሪ አባላት ውስጥ ኢንጅንር ጌዴዎን አስፋው፣ ዶክተር ያዕቆበ አርሳኖ፣ አቶ ዘሪሁን አበበ እንዲሁም ሌሎች ኢትዮጵያዊያን ተሳትፈዋል።
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.