Fana: At a Speed of Life!

የኤሌክትሪክ ቆጣሪ እናስገባለን በሚል ሰበብ ህገወጥ ድርጊት የሚፈፅሙ ግለሰቦች ስላሉ ህብረተሰቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ተቋሙ አሳሰበ

አዲስ አበባ፣ ጥር 24፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኤሌክትሪክ ቆጣሪ እናስገባለን በሚል ሰበብ ህገወጥ ድርጊት የሚፈፅሙ ግለሰቦች ስላሉ ህብረተሰቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አሳሰበ፡፡

ከኤሌክትሪክ አገልግሎት ጋር ተያይዞ ለሚቀርቡ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጠውም ይህ ተቋም ቢሆንም ከህጋዊ አሰራር ውጭ የተቋሙ ሠራተኛ በመምሰል እኩይ ዓላማ ያነገቡ ግለሰቦች የኤሌክትሪክ ቆጣሪ እናስገባለን በሚል ሽፋን በህገ-ወጥ መንገድ ከህብረተሰቡ ገንዘብ እንደሚቀበሉ ማረጋገጡን ነው ተቋሙ የገለጸው፡፡

ለአብነትም ነዋሪነቷ በአዲስ አበባ ከተማ በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 07 የሆነች አንዲት ግለሰብ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የማያውቀው ነገር ግን “ከተቋሙ ነው የመጣነው ቆጣሪ እናስገባልሻለን” ብለው በማታለል ገንዘብ ተቀብለዋት ህጋዊ ያልሆነ የኤሌክትሪክ ቆጣሪ ገጥመውላታል፡፡

ግለሰቧ ለእነዚህ ሰዎች በሐሰተኛ እሴት ታክስ ደረሰኝ 12 ሺህ ብር የከፈለቻቸው ቢሆንም ድርጊቱ ከተቋሙ እውቅና ውጪ እንደነበር ነው የተጠቀሰው፡፡

በመጨረሻም በተደረገው ማጣራት የተገጠመው ቆጣሪ ህገወጥና ትክክለኛውን የአሰራር ስርዓት ተከትሎ የተፈፀመ አለመሆኑን ተደርሶበት  የተገጠመላት ቆጣሪ አገልግሎት እንዳይሰጥ መደረጉንም ነው የተገለጸው፡፡

ህብረተሰቡ እንደነዚህ አይነት መሰል እኩይ ድርጊቶች ሊያጋጥመው ስለሚችል አስፈላጊ ጥንቃቄ እንዲወስድ ተቋሙ በአንፅንኦት ያሳስባል፡፡

ተቋሙ የአዲስ ቆጣሪ ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥበት የራሱ የሆነ የአሰራር ስርዓት የዘረጋ መሆኑ ታውቆ፤ ህብረተሰቡ መሰል ጥያቄም ሆነ ሌሎች ከኤሌክትሪክ አገልግሎት ጋር ተያይዞ ለሚያቀርበው ማንኛውንም ጥያቄ በአቅራቢያ ወደሚገኘው የተቋሙ አገልግሎት መስጫ ማዕከል በአካል በመሄድ በማመልከት መገልገል እንደሚቻል ከተቋሙ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤

ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ

ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ

ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.