Fana: At a Speed of Life!

ጁንታው በቀን እስከ 25 ሺህ የሀሰት መረጃዎችን በቲውተር ሲሰራጭ እና የሚዲያዎችን ስርጭት ለማስተጓጎል ሲሰራ እንደነበረ ተገለጸ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 2፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በህወሓት ጁንታ ቡድን አማካይነት በቀን እስከ 25 ሺህ የሀሰት መረጃዎችን በቲውተር ሲሰራጭ የነበረ ሲሆን፤ ኢቢሲ߹ ዋልታ እና ኦቢኤን የጥቃት ኢላማዎቹ ሲሆኑ፣ የፋና እና የሌሎች ሚዲያዎች ስርጭት እንዲቋረጥ ሲሰራ እንደነበረ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ገለጸ።

በህወሀት ጁንታ ቡድን የማህበራዊ ትስስር ገጾችን በመጠቀም ከፍተኛ የሆነ የስነ-ልቦና ጦርነቶችን ሲያከናዉን እንደነበር የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ከፍያለዉ ተፈራ ገለጹ፡፡

ሃገሪቷን ወደ ለየለት ትርምስ ለማስገባት ጁንታዉ የሳይበር ምህዳሩን በመጠቀም ከፍተኛ የማወናበድ ስራ ሲሰራ እንደነበርም ሃላፊዉ ተናግረዋል፡፡

ጁንታው የዲጂታል ወያኔ የተባለ የሃሰት መረጃዎችን የሚያሰራጭ ቡድን በማቋቋም በበላይነት ሲመራ እንደነበር ያነሱት ሃላፊዉ የሳይበር ተፋላሚዎችን በመቅጠር የኦሮሞ ብሄር ተወላጅ መስለው አማራን ߹ የአማራ ብሄር ተወላጅ መስለው ደግሞ የኦሮሞን ስም ሲያጠለሹ መቆየታቸዉን አንስተዋል፡፡

ጥቀምት 24 በመከላከያ ሰራዊታችን ላይ ጥቃት ከማድረሳቸው በፊት ከመሃል ሃገር የሚደረጉ ግንኙነቶች እንዳይኖሩ የመገናኛ ስርዓቱን ከጥቅም ዉጪ ማድረጋቸውን የገለጹት አቶ ከፍያለው ከዛም ባለፈ ቲዊተርን በመጠቀም የሃሰት መረጃ በማሰራጨት ከፍተኛ የሆነ የስም ማጥፋት ዘመቻዎችን ሲያከናዉኑ መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡

በዚህ የሃሰት ፕሮፖጋንዳ ከተለያዩ ብሄር ጽንፈኛ የሆኑ ደጋፊዎቻቸዉን እና የዉጭ ዜጋ ሆነዉ ከዚህ ቀደም የጥቅም ትስስር የነበራቸዉን አካላትን በማደራጀት የዘመቻዉ አካል እንዳደረጓቸዉ ያስታወሱት ም/ዋና ዳይሬክተሩ በዚህ ዘመቻም በቀን እስከ 25 ሺህ ሃሰተኛ ቲዊቶችን ߹ የሃሽታግ አካዉንቶችን በመክፈት ደግሞ በቀን ከ13 ሺህ እስከ 18 ሺህ ሃሰተኛ መረጃዎችን ሲያሰራጩ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

በዚህ የሃሰት ፕሮፖጋንዳም የህግ ማስከበር ሳይሆን ግዛት ማስፋፋት ተግባር አድርጎ የማቅረብ፣ በጦርነቱ ንጹሃን በከፍተኛ ሁኔታ እየተጨፈጨፉ እንደሆኑ የማስተጋባት፣ በትግራይ ተወላጆች ላይ የዘር ማጥፋት ዘመቻ እየተፈጸመ እንደሆነና በመላዉ ሃገሪቱ የትግርኛ ተናጋሪዎች ተነጥለዉ የጥቃት ኢላማ እንደሆኑ በማስመሰል መዘገብን ይገኙበታል፡፡

መንግስት በጁንታው ቡድን ላይ የህግ ማስከበር ተግባር መጀመሩን ተከትሎ የተለየ የሳይበር ጥቃት እንዳልተከሰተ ያነሱት አቶ ከፍያለዉ ሆኖም በዓለም አቀፍ ደረጃ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከሰቱን ተከትሎ ብዙዎቹ በቤታቸው ሆነው በኦንላይን እየሰሩ ባለበት ሁኔታ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከተጠበቀዉ በላይ በ3 እጥፍ የሳይበር ጥቃት መጨመሩን ጠቅሰዋል፡፡

በህግ ማስከበር ዘመቻዉ ወቅት የህወሃት ጁንታው ቡድን የዲ ደብሊዩን እና የትግራይ ቲቪ ፍላይ አዌይ ስርዓትን በመጠቀም ግዙፍ የሃገሪቱን የሚዲያ ተቋማት አገልግሎት ለማቋረጥ ሙከራ እንዳደረገ ሃላፊዉ ጠቁመዋል፡፡

የዚህ ጥቃት ኢላማ ከነበሩ ሚዲያዎች መካከልም ኢቢሲ߹ ዋልታ እና ኦ ቢ ኤን ዋናዎቹ እንደነበሩ ያነሱት ሃላፊዉ ፋና እና ሌሎች መሰል ሚዲያዎችን ስርጭት የማቋረጥ ተግባር የመፈጸም አዝማሚያ እንደነበር ሃላፊዉ አስታውሰዋል፡፡

ሆኖም ኤጀንሲዉ በወሰደዉ ቅድመ መከላከል በሚዲያዎቹ ላይ ሊደርስ የታሰበውን የጠለፋ ተግባር ለማክሸፍ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡

ከዲጂታል ወያኔ በተጨማሪ ሌሎች የጥቅም ተጋሪዎች በጥፋት ዘመቻዉ ተሳታፊ እንደነበሩ የገለጹት ም/ዋና ዳይሬክተሩ በግለሰቦች ደረጃ ከ50 እስከ 500 የሚደርሱ ሰዎችን በስራቸዉ በማሰማራት እና ክፍያ በመፈጸም ጥቃት ለማድረስ መሞከሩን ነዉ ያነሱት፡፡

በአዲስ አበባ ዉስጥም አንድ ለአምስት እና አንድ ለሃያ አደራጅተዉ አጀንዳ እየሰጡ ብሄርን ከብሄር ህዝብን ከህዝብ ሲያጋጩ የሚዉሉ ሃይሎች መኖራቸው እንደተደረሰበት አቶ ከፍያለዉ ጠቁመዋል፡፡

ከዚህም ባለፈ በዉጭ ሃገራት ከሚገኙ ጽንፈኛ ቡድኖች እና ሚዲያዎች ጋር በመናበብ የተለያዩ የጥፋት እንቅስቃሴዎችን ሲያከናዉኑ ነበር ያሉት ሃላፊዉ ለአብነትም ኦ.ኤም.ኤን ቲቪን ጨምሮ ኢትዮ-360 ከሚባል የማህበራዊ ትስስር ገጽ ጋር ሲሰሩ መቆየታቸዉን ገልጸዋል፡፡

በመሆኑም ህብረተሰቡ የሳይበር ምህዳሩን በመጠቀም ከሚሰራጩ የሀሰተኛ መረጃዎች እራሱን በመጠበቅ ትክክለኛዉን መረጃ ከሚመለከተዉ አካል ብቻ ለማግኘት መሞከር አለበት ብለዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.