Fana: At a Speed of Life!

ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ የጅቡቲን የመጨረሻ ከፍተኛ ወታደራዊ ኒሻን ተሸለሙ

አዲስ አበባ ፣ ጥር 1 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢፌዴሪ መከላከያ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ ከጂቡቲ መከላከያ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል ዘካሪያ ሼህ ኢብራሂም የሃገሪቱን የመጨረሻ ከፍተኛ ወታደራዊ ኒሻን ተበረከተላቸው።

በኒሻን ማልበስ ስነስርዓቱ የተገኙት የሰላም ማስከበር ማዕከል ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቼ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንደገለፁት፣ ጄኔራል ብርሃኑ ከጂቡቲ መንግስት የተበረከተላቸው ኒሻን በሃገሪቱ ፕሬዚዳንት ተፈቅዶ የተሰጣቸውና የመጨረሻ ከፍተኛ ደረጃ ኒሻን ነው።

ጄኔራል ብርሃኑ በወታደራዊ የአመራር ክህሎታቸው ባሳዩት ድንቅ የመሪነት ብቃት በሃገሪቱ አጋጥሞ የነበረው አደጋ እንዲቀለበስ በማድረግና ህግ የማስከበሩን ተግባር መከላከያ ሰራዊት በአኩሪ ጀግንነት እንዲፈፅም የመሪነት ሚናቸውን በመወጣት ኢትዮጵያንና የአካባቢው ሃገራት ከተጋረጠባቸው ከፍተኛ አደጋ በማዳናቸው እንደተበረከተላቸው ገልፀዋል።

በኒሻን ማልበስ ስነስርዓቱ የጂቡቲ መከላከያ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል ዘካሪያ ሼህ ኢብራሂም፣ የጄኔራል ብርሃኑ ጁላን የመሪነት ብቃት አድንቀው፣ ጉዳቱን መከላከል ባይቻል ኖሮ ኢትዮጵያን በመበተን ብቻ ሳይቆም የአካባቢውን ሃገራት የሚበትን አደገኛ ሁኔታ ያጋጥም ነበር ብለዋል።

ጄኔራል ዘካሪያ ሼህ ኢብራሂም ጂቡቲና ኢትዮጵያ ያላቸው ታሪካዊ ወዳጅነት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በስነስርዓቱ አረጋግጠዋል።

ሽልማቱ የተበረከተላቸው የኢፌዴሪ መከላከያ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ የሃገሪቱን ከፍተኛ የመጨረሻ ኒሻን ላበረከተላቸው የጂቡቲ ህዝብና መንግስት በኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊትና በኢትዮጵያ ህዝብ ስም ምስጋና ማቅረባቸውን የሰላም ማስከበር ኃላፊው ሌተናል ጄኔራል ደስታ ገልፀዋል።

በስነስርዓቱ ሃገራቱን የሚወክሉ የተለያዩ የድል መዝሙሮች መቅረባቸውንና የሃገራቱ የሁለትዮሽ ውይይት መደረጉን ኢዜአ ዘግቧል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.