Fana: At a Speed of Life!

21 ሺህ 695 የጋራ መኖርያ ቤቶችና ከ13 ሚሊየን በላይ ካሬ መሬት በህገወጥ መንገድ መያዛቸው መረጋገጡን ወ/ሮ አዳነች ገለፁ

አዲስ አበባ፣ ጥር 18፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ) አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ ከመሬት ወረራና ባለቤት አልባ ህንፃዎች እንዲሁም ከኮንዶሚኒየምና የቀበሌ ቤቶች ዙሪያ የተደረገ የማጣራት ውጤት ላይ መግለጫ እየሰጡ ነው።

በመግለጫቸውም  በአጠቃላይ በከተማችን 13 ሚሊየን 389 ሺህ 955 ካሬ ወይም 1 ሺህ 338 ሄክታር መሬት በህገወጦች መያዙን አስታውቀዋል።

በከተማዋ የተፈፀመው የመሬት ወረራ የከረመ ታሪክ ያለውና በየጊዜው እየተደራረበ የመጣ ህገወጥ ድርጊት ነው ያሉት ምክትል ከንቲባዋ በዚህ ጥናት ላይ እንደተመላከተው ከ1997 ጀምሮ በከተማዋ በተለያየ አግባብ ህገወጥ የመሬት ወረራው ሲፈፀም የነበረ ብለዋል፡፡

በ2010 ሀገራዊ ለውጥ ከመምጣቱ በፊት ሰፋ ባለ መልኩ የመሬት ወረራው የነበረና ከለውጡ በኋላም አጠቃላይ አመራሩ ህገወጥነትን በተገቢው ባለመከላከሉ ችግሩ እንዲደራረብ አድርጎታል ነው ያሉት።

ባለቤት አልባ ቤቶችና ህንፃዎች በተመለከተም ባለቤት አልባ በሚል የተለዩት ቤቶችና ህንፃዎች በድምሩ 322 ሲሆኑ፣ የቦታ ስፋታቸው ደግሞ 229 ሺህ 556 ካሬ መሆኑ ተለይቷል ብለዋል፡፡

በከተማዋ ህገወጥ የመሬት ወረራ ባህሪያት ጋር በተያያዘ በህገወጥ መንገድ ባዶ የሆነ የመንግስትን መሬት በወረራ በመያዝ የተፈፀመ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን ይህ ድርጊት በግለሰብ ደረጃና በሀይማኖት ተቋማትም ጭምር የተፈፀመ መሆኑ ምክትል ከንቲባዋ ተናግረዋል።

በህገወጥ መልኩ የመንግስትና የህዝብን መሬት በቡድን በመሄድና ፣ በህገወጥ መልኩ ይዞታን በማስፋፋት የመንግስትን መሬት በመውረር  መሆኑ ተጠቁሟል።

የኮንደሚኒየም ቤቶችን በተመለከተም በተካሄደው ጥናት ውጤት መሰረት  በህገወጥ መንገድ የተያዙ የጋራ መኖርያ ቤቶች በጠቅላላው 21 ሺህ 695 ሲሆኑ 15 ሺህ 891 የጋራ መኖሪያ ቤቶች መረጃ ያልቀረበባቸው  እንደሆኑ ተናግረዋል።

4 ሺህ 530 ባዶ የሆኑ፣ 850 ዝግ የሆኑ ፣ እና 424 በህገወጥ መልኩ በግለሰቦች ተይዘው የሚገኙ ሲሆን በዕጣ ሳይሆን በተለያዪ አግባቦች ወደ ተጠቃሚው ግለሰቦች የተላለፉ ደግሞ 51 ሺህ 64 ቤቶች ሆነው ተገኝተዋል፡፡

በቤቶች ኮርፖሬሽን ተመዝግቦ የሚገኘው ባለዕጣዎች የስም ዝርዝር እና በመስክ በተገኘው የተጠቃሚዎች የስም ዝርዝር መሀከል ልዩነት ያላቸው ቤቶች 132 ሺህ 678 እንደሆኑና 18 ሺህ 423 ቤቶች ደግሞ የቤት ባለቤት ስም የሌላቸው መሆኑን በጥናቱ ተለይቷል፡፡

በእነዚህ ቤቶች ውስጥ የሚኖሩ ግለሰቦች መረጃቸውን እንዲያቀርቡ በተደጋጋሚ ቢጠየቁም መረጃ ማቅረብ ያልቻሉ ወይም ያልፈለጉ በመሆናቸው ቤቶቹ በህገወጥ መንገድ የተያዙ መሆናቸውም በጥናቱ ተለይቷል ፡፡

ያልተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶችና የጋራ መጠቀሚያ ህንፃዎች ሁኔታ በተመለከተ 28 ብሎክ ማለትም ከ782 እስከ 842 የሚሆኑ ቤቶች እና የጋራ መጠቀሚያ ህንፃዎች (ኮሚናል ) ደግሞ 83 ሳይገነቡ መቅረታቸውን ጥናቱ ማመላከቱ ተገልጿል፡፡

በፌደራልና በአዲስ አበባ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤቶች በተሰራው የኦዲት ውጤት መሰረትም በአጠቃላይ ላልተገነቡ ህንፃዎች የቦርድም ሆነ የስራ አመራር የውሳኔ ቃለ ጉባኤ አልተገኘም።

ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች ምንም እንኳን መረጃ ባይገኝም ለግንባታው ክፍያ አልተከፈለም ብሎ መደምደም እንደሚያስቸግር በኦዲት ጥናቱ ማመልከቱን ገልፀዋል፡፡

ከየወረዳ ቤቶች ልማት ጽህፈት ቤቶች በተገኘ መረጃ መሰረት አጠቃላይ በከተማ አስተዳደሩ ስር የሚተዳደሩ 150 ሺህ 737 የቀበሌ መኖሪያ እና ንግድ ቤቶች አሉ፡፡

በዚህ ጥናት ተደራሽ መሆን የተቻለው 138 ሺህ 652 የመኖሪያ እና የንግድ ቤቶች ናቸው፡፡

በከተማዋ 10 ሺህ 565 የቀበሌ ቤቶች በቁልፍ ግዥ፣ ሰብሮ በመግባት፣ እና በሌሎች ህጉ ከሚፈቅደው ውጪ በህገ-ወጥ መንገድ ተይዘዋል ብለዋል ምክትል ከንቲባዋ፡፡

በጥናቱ ተደራሽ ከተደረጉ የቀበሌ መኖሪያ ቤቶች ውስጥ፡-

1.7 ሺህ 723 ቤቶች ውል በሌላቸው (ህገወጥ) በሆኑ ሰዎች ተይዘዋል፡፡

  1. 2 ሺህ 207 የቀበሌ ቤቶች ወደግል የዞሩ፣
  2. 265 በሶስተኛ ወገን የተያዙ፣
  3. 164 ኮንደምንየም በደረሳቸው/የራሳቸው ቤት ባለቸው ሰዎች የተያዙ

የቀበሌ መኖሪያ ቤቶች መኖራቸው ነው፡፡

  1. 137 ለመኖሪያነት የሚያገለግሉ የቀበሌ ቤቶች በሽያጭ ወደ ግል የተላለፉ፤
  2. 1 ሺህ 243 ታሽገው/ተዘግተው የተቀመጡ፣
  3. 5 ሺህ 43 የፈረሱ፤
  4. 180 አድራሻቸው የማይታዎቁ/የጠፉ የቀበሌ መኖሪያ ቤቶች እንዳሉ ተረጋግጧል፡፡

የቀበሌ ንግድ ቤቶችን በተመለከተ በሰጡት በመግለጫ በአጠቃላይ የንግድ ቤቶች ብዛታቸው 25 ሺህ 96 ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ በህገወጥ መንገድ የተያዙ የቀበሌ የንግድ ቤቶች ብዛት 4 ሺህ 76 ናቸው።

  1. 1 ሺህ 70 የንግድ ቤቶች ውል የሌላቸው ነጋዴዎች እየተጠቀሙባቸው

መሆኑ ተለይቷል

  1. 2 ሺህ 451 የቀበሌ የንግድ ቤቶች ከአንድ በላይ የንግድ ቤት በያዙ

1,086 ነጋዴዎች እንደተያዙ ተለይቷል

  1. 376 የቀበሌ ንግድ ቤቶች ደግሞ በተከራይ ተከራይ በሶስተኛ ወገን

መያዛቸው ተለይቷል፣

  1. 179 የታሸጉ የንግድ ቤቶች እንዳሉም ለመለየት ተችሏል፡፡

በአላዛር ታደለ

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤

ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ

ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ

ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.