Fana: At a Speed of Life!

24 የአልሸባብ አመራሮችን ጨምሮ ከ800 በላይ የቡድኑ ተዋጊዎች ተደመሰሱ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 29፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የጸጥታ ኃይሉ በወሰደው እርምጃ እስካሁን ባለው ሂደት 24 የአልሸባብ አመራሮችን ጨምሮ ከ800 በላይ የሽብር ቡድኑ ተዋጊዎች መደምሰሳቸውን ጊዜያዊ የጸጥታ ኮማንድ ፖስት አስታወቀ፡፡

የመከላከያ ኃይል ስምሪት ኃላፊና የጊዜያዊ ኮማንድ ፖስቱ አስተባባሪ ሜጀር ጄነራል ተስፋዬ አያሌው እና የሶማሌ ክልል ልዩ ኃይል አዛዥ ኮሚሽነር ጄነራል መሃመድ አህመድ ለኢዜአ እንደተናገሩት ፥ የአልሸባብ የሽብር ቡድን ከሐምሌ 14 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ኢትዮጵያ ሰርጎ ለመግባት ያደረገው ሙከራ በፀጥታ ኃይሉና በሕዝቡ የተቀናጀ እርምጃ ሙሉ በሙሉ ከሽፏል።

ድሽቃን ጨምሮ በርካታ የቡድንና የነፍስ ወከፍ መሳሪያዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውም ነው የተገለጸው፡፡

ሜጀር ጄኔራል ተስፋዬ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያን ለማተራመስ የሚሹ የውጭ ጠላቶች የውስጥ ባንዳዎችን በመቅጠር ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡

እቅዳቸው እንዳሰቡት አልሳካ ሲላቸው በአሁኑ ወቅት አልሸባብን ከኋላ በመደገፍ ከንቱ ሙከራ ማድረጋቸውንም ነው ያብራሩት፡፡

ይህም ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ጸጋዎችን ተጠቅማ ለመልማት የጀመረችውን ተስፋ ሰጪ ሥራ ለማደናቀፍ ያለመ ሙከራ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

በዚህም አልሸባብ ኢትዮጵያና ሶማሊያ በሚዋሰኑባቸው አካባቢዎች የተወሰነ ኃይሉን በ16 ተሽከርካሪዎች በመጫንና የተወሰነውን ደግሞ ጨለማን ተገን አድርጎ በእግር ወደ ኢትዮጵያ ሰርጎ በማስገባት ጥቃት ለመፈጸም መሞከሩን ነው የገለጹት፡፡

ሆኖም የመከላከያ ሰራዊቱ ከሶማሌ ክልል ልዩ ኃይል ጋር በመቀናጀት በወሰደው እርምጃ ወደ ኢትዮጵያ ሰርጎ ለመግባት የሞከሩ የሽብር ቡድኑ አመራሮችን ጨምሮ ተዋጊዎቹ ሙሉ ለሙሉ ተደምስሰዋል ነው ያሉት፡፡

የኢፌዴሪ አየር ኃይል የተመረጡ ዒላማዎችን ነጥሎ በመምታት የሽብር ቡድኑ ለረዥም ጊዜ እጠቀምበታለሁ ብሎ ያዘጋጀውን የሎጂስቲክስና ጦር መሳሪያ ክምችት ማውደሙ የተገለጸ ሲሆን ፥ የሽብር ቡድኑን አመራሮችም መደምሰስ መቻሉ ተገልጿል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.