በተለያዩ ሀገራት በተካሄዱ የአትሌቲክስ ውድድሮች ላይ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ድል ቀንቷቸዋል
አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 11፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት በዓለም አቀፍ ደረጃ በተለያዩ ሀገራት በተካሄዱ የጎዳናና የአገር አቋራጭ የአትሌቲክስ ውድድሮች ላይ የተሳተፉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ድል ቀንቷቸዋል፡፡
በታይዋን በተደረገ የታይፒ ማራቶን ውድድር በወንዶች ደመቀ ካሰው 2 ሰአት ከ11 ደቂቃ ከ41 ሰከንድ በመግባት ውድድሩን በበላይነት ሲያጠናቅቅ መሰረት አራጋው 2 ሰአት ከ14 ደቂቃ ከ59 ሰከንድ በሆነ ሰዓት ውድድሩን በሁለተኝነት አጠናቋል፡፡
በሴቶች አለምፀሃይ አሰፋ 2 ሰአት ከ30 ደቂቃ ከ44 ሰከንድ በመግባት አሸናፊ መሆኗን የኢትዮፕያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ ያመላክታል።
በጃፓን በተደረገ የሳንዮ ሴቶች ግማሽ ማራቶን ውድድር ደግሞ አትሌት ዘይቱና ሁሴን 1 ሰአት ከ9 ደቂቃ ከ31 ሰከንድ በሆነ ጊዜ በመግባት አንደኛ ስትወጣ፣ አትሌት ደስታ ቡርቃ ውድድሩን በሁለተኛ ደረጃ አጠናቃለች፡፡
በሌላ በኩል በጣሊያን ሲታዴላ በተደረገ ሲታ ሙራታ ግማሽ ማራቶን ውድድር በሴቶች አዲስዓለም በላይ 1 ሰአት ከ12 ደቂቃ ከ7 ሰከንድ በሆነ ሰዓት ውድድሩን በበላይነት አጠናቃለች፡፡
እንዲሁም በስፔን በተደረገ ኢንትርናሲኦናል ዲ ቬንታ ዲ ባኖስ አገር አቋራጭ ውድድር በወንዶች 10 ሺህ 575 ሜትር አትሌት ንብረት መላክ 32 ደቂቃ ከ37 ሰከንድ በሆነ ጊዜ በመግባት ውድድሩን በሁለተኝነት ሲያጠናቅቅ፥ በሴቶች 7 ሺህ 975 ሜትር ውድድር ደግሞ አትሌት ልቅና አምባው በ29 ደቂቃ ከ53 ሰከንድ በመግባት ውድድሩን በሁለተኝነት አጠናቃለች፡፡
አካባቢዎን ይጠብቁ!
ወደ ግንባር ይዝመቱ!
መከላከያን ይደግፉ!
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!