Fana: At a Speed of Life!

አሸባሪው የህወሓት ወራሪ በተቋማት ላይ የፈጸመው ጥቃት ተራ ዘረፋና ውድመት ሳይሆን ሀገርን የማዳከም እቅድ ነው – አቶ ደመቀ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 12፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) አሸባሪው የህወሓት ወራሪ በተቋማት ላይ የፈጸመው ጥቃት ተራ ዘረፋና ውድመት ሳይሆን ሀገርን የማዳከም እቅድ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ገለጹ።
 
አቶ ደመቀ በደሴና ኮምቦልቻ ከተሞች ጉዳት የደረሰባቸውን ሆቴሎች፣ የደሴ ግብርና ቲሹ ካልቸር ማዕከል፣ የወሎ ዩኒቨርሲቲ፣ የኮምቦልቻ ሆስፒታልና ችፑድ ፋብሪካን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።
 
የደሴ ግብርና ቲሹ ካልቸር ማዕከል የደረሰበት ውድመት ሆነ ተብሎ አካባቢውን ብሎም ሀገርን ከድህነት የመውጣትና ቴክኖሎጂን የማዘመን እቅድ ወደኋላ እንዲጎተት ታልሞ እንዲወድም የተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
 
ማዕከሉ ከጅምሩ በደሴ ከተማ እንዳይቋቋም ብዙ ጫና ሲደረግ እንደነበርም አስታውሰው፤ በብርቱ ጥረትና በተለያዩ አካላት ርብርብ መመስረቱን ገልጸዋል።
 
በተመሳሳይ የኮምቦልቻ ችፑድ ማምረቻ የሀገሪቱን የወጪ ንግድ አቅም ማሳደግ የሚችል ዘመናዊ ፋብሪካ ላይ የደረሰው ውድመት መሆኑን ጠቁመዋል።
 
በመሆኑም በነዚህና መሰል ግዙፍ ሀገራዊ ተቋማት ላይ የደረሰው ጥቃት ተራ ዘረፋና ውድመት ሳይሆን ሀገርን በኢኮኖሚ የማዳከምና የማጥፋት አጀንዳ ነው ብለዋል።
 
እንደዚህ አይነት ተቋማት በምንም ሁኔታ ተበትነው እንደማይቀሩ የገለጹት አቶ ደመቀ፤ መልሶ በማደራጀትና በመገንባት የታሰበውን የማውደም ወረራ መቀልበስ ይገባል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
 
በቀጣይም የጥፋት ቡድኑን ለይቶ ማውጣት፣ የጉዳት መጠኑን መለየትና የክልልና የፌደራል መንግስታት በመተባበር መልሶ ማቋቋም የሚችሉበት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.