ዓለምአቀፋዊ ዜና

የሱዳን ጦር ኢብራሂም ኤልባዳዊን ጠቅላይ ሚኒስትር አድርጎ ሊሾም ነው

By Alemayehu Geremew

January 03, 2022

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 25፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የሱዳን ጦር የቀድሞ የሀገሪቷ ገንዘብ ሚኒስትር የነበሩትን ኢብራሂም ኤልባዳዊ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርጎ ሊሾም መሆኑን ሲጂቲኤን አስነብቧል፡፡

አብደላ ሀምዶክ ከጠቅላይ ሚኒስትርነታቸው መልቀቃቸውን ይፋ ማድረጋቸውን ተከትሎ ነው የሀገሪቱ ጦር ኢብራሂም ኤልባዳዊን በቦታው ሊተካቸው መሆኑ የተሰማው።

ኢብራሂም ኤልባዳዊ ከፈረንጆቹ ጥር 2017 ጀምሮ እስከ ነሐሴ 2019 የሀገሪቷ የምጣኔ ሀብት ምርምር መድረክ አሥተዳደር ዳይሬክተር በመሆን አገልግለዋል፡፡

በካርቱም ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ያገለገሉትና ጡረታ የወጡት ፕሮፌሰር ኢብራሂም ኤልባዳዊ ፥ የጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሀምዶክ የካቢኔ አባል በመሆን ከፈረንጆቹ መስከረም 2019 እስከ ሐምሌ 2020 የሀገሪቷ የፋይናንስና የኢኮኖሚ ፕላን ሚኒስትር በመሆን ማገልገላቸውም ነው የተመለከተው፡፡

ከሀገራቸው በተጨማሪም በዱባይ የምጣኔ ሐብት ምክር ቤት የምጣኔ ሐብት ፖሊሲ እና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር በመሆን፣ በዓለም ባንክ የልማት ጥናትና ምርምር ቡድን መሪ በመሆን ሰርተዋል፡፡

ኢብራሂም ኤልባዳዊ ከሰሜን ካሮላይና እና ከሰሜን ምዕራብ አሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች በምጣኔ ሐብት እና በስታትስቲክስ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ማግኘታቸውንም ከ”ኢኮኖሚክ ሪሰርች ፎረም” ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡