የሀገር ውስጥ ዜና

የአገራዊ የምክክር ኮሚሽንን እንዲመሩ የሚጠቆሙ ግለሰቦችን አቅም እና ችሎታ በጥንቃቄ ማጤን እንደሚገባ ምሁራን ገለጹ

By Meseret Awoke

January 17, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥር 9፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የአገራዊ የምክክር ኮሚሽንን በኮሚሽነርነት እንዲመሩ የሚጠቆሙ ግለሰቦችን አቅም እና ችሎታ በጥንቃቄ ማጤን እንደሚያስፈልግ ምሁራን ገለጹ።

የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት አመራሮች የሆኑት አህመድ ሁሴን እና ትነበብ ብርሃኔ ከፋና ቴሌቪዥን ጋር ቆይታ አድርገዋል፡፡

ምሁራኑ በቆይታቸው እንደተናገሩት፥ ሀገርን በቀውስና በጥላቻ ውስጥ ያየየንና ለዓመታት የተጠራቀመ ችግርን በግልጽ ወደፊት አምጥቶ ለምክክር እና መፍትሄውንም በጋራ ለማስቀመጥ የተቋቋመው አገራዊ የምክክር ኮሚሽን÷ ነፃ እና ገለልተኛ ሆኖ ተግባራቱን በስኬት እንዲያከናውን ማድረግ ይገባል፤ ለዚህም ኮሚሽኑን ለመምራት በዜጎች የሚጠቆሙ ግለሰቦች አገራዊ ምልከታ እና ብቃት በአንክሮ ሊጤን እንደሚገባ አስምረውበታል።

አግላይና አካታች ያልሆነው የቀደመው መንገድ አገርራችንንና ህዝባችንን ዋጋ እንዳስከፈለ የሚገልጹት ምሁራኑ፥ አሁንም የጋራ የሆነውን አገራዊ የምክክር ኮሚሽን እንዲመሩ ለሃላፊነት የሚታጩ ወገኖች ለነገ የጋራ ድልም ሆነ ችግር ወሳኝ እንደሆኑ ተናግረዋል።

ጉዳዩ የእያንዳንዱን ዜጋ ህይወት የሚነካ አገራዊ አጀንዳ እንደመሆኑ የሁሉንም ዜጋ ትኩረት እና ሃላፊነት የሚጠይቅ እንደሆነ ነው የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች አመራሮቹ ያሳሰቡት።

ለጥቆማ የተሰጠው ጊዜ መራዘሙ ብቁ ሰዎችን ለመጠቆም እንዲቻል እድል የፈጠረ እንደሆነም ተናግረዋል።

ለአገራዊ የምክክር ኮሚሽን የኮሚሽነሮች የጥቆማ ጊዜ እስከ መጪው ጥር 13 የሚቆይ ሲሆን፥ በቀረው አጭር ጊዜ ውስጥ ዜጎች ኮሚሽኑን በገለልተኛነት እና በትልቅ ሃላፊነት ለማገልገል አቅም እና ችሎታ ያላቸውን ግለሰቦች እንዲጠቁሙ ጠይቀዋል።

በፍሬህይወት ሰፊው

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፤ እንገንባ፤ እንዘጋጅ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!