የቤልጂየም ባለሐብቶች በተለያዩ ዘርፎች ላይ በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ተጠየቀ
አዲስ አበባ፣ የካቲት 17፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) አምባሳደር ሂሩት ዘመነ በንግድ፣ ቱሪዝም እና ኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ በትብብር መሥራት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ከዋሎኒያ በአፍሪካ እና በመካከለኛው ምስራቅ ወጪ ንግድ እና ኢንቨስትመንት ዳይሬክተር ከሆኑት ኤሪክ ዲ ሴኢሌኢስኪ ጋር ፍሬያማ ውይይት ማካሄዳቸውን ገለጹ፡፡
አምባሳደር ሂሩት በበይነ -መረብ ባካሄዱት ውይይት የቤልጂየም ኩባንያዎች በኢትዮጵያ በተለያዩ ዘርፎች ላይ መዋዕለ-ንዋያቸውን ቢያፈሱ ምቹ ምህዳር እንደሚፈጠርላቸው ገለጻ አድርገውላቸዋል፡፡
አምባሳደሯ በቀጣይ ኢትዮጵያ ወደ ኢንዱስትሪ-መር ኢኮኖሚ ሽግግር እያደረገች እንደሆነና ለዚህም በርካታ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን እና ፋብሪካዎችን እንደገነባች ጠቁመዋል፡፡
ኤሪክ ዲ ሴኢሌኢስኪ በበኩላቸው የቤልጂየም ባለሐብቶች በአፍሪካ መዋዕለ-ንዋያቸውን ለማፍሰስ ከፍተኛ ፍላጎት እና ተነሳሽነት አላቸው ብለዋል፡፡
በዚህ ዓመትም በርካታ የቤልጂየም ኩባንያዎች በአፍሪካ የንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ ለመሳተፍ ቁርጠኛ ናቸው ብለዋል፡፡
በቀጣይ በፋርማሲው ዘርፍ ያለውን የሥራ ዕድል ለመቃኘት ፣ የሀገራችንን የቡና ወጪ ንግድ ለማስፋት ብሎም በቱሪዝም ዘርፍ ላይ ለመሥራት ስምምነት ላይ መደረሱን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ አመልክቷል፡፡