በጋሞ ዞን 400 ሚሊየን ብር በሚጠጋ ወጪ ለሚገነባው ትምህርት ቤት የመሠረት ድንጋይ ተጣለ
አዲስ አበባ፣ የካቲት 23፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በጋሞ ዞን አስተዳደር 400 ሚሊየን ብር በሚጠጋ ወጪ ለሚገነባው የሁለተኛ ደረጃ ሞዴል ትምህርት ቤት የመሠረት ድንጋይ ተጣለ።
የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ ትምህርት ቤቱ ትውልድን በመቅረጽ ሀገርን መረከብና መመራመር የሚችሉ እና የበለጸገች ኢትዮጵያን ዕውን የሚያደርጉ የምጡቅ አዕምሮ ባለቤት የሆኑ ተማሪዎች የሚማሩበት ሞዴል ትምህርት ቤት ይሆናል ብለዋል።
የትምህርት ቤቱን ግንባታ በአጭር ወራት ውስጥ በማጠናቀቅ በቀጣይ ዓመት የተለየ ችሎታ እና ተሰጥኦ ያላቸው እንዲሁም በተለያየ ምክንያት የመማር እድል ያላገኙ ተማሪዎች እንዲማሩበት እንደሚደረግ አቶ ብርሃኑ ተናግረዋል።
የደቡብ ክልል ብልጽግና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጥላሁን ከበደ በበኩላቸው ትምህርት ቤቱ ከፍተኛ ውጤት የሚያመጡ ብቻ ሳይሆኑ ተመራምረው ለሀገር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያበረክቱ የሚችሉ ተማሪዎች የሚፈልቁበት እንደሚሆን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
ግንባታውን የኦሮሚያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን የሚያከናውነው ሲሆን ትምህርት ቤቱ በ16 ሄክታር ላይ የሚያርፍና 25 ብሎኮች ያሉት ነው።
ልዩ ትምህርት ቤቱ የመማሪያ ክፍሎች ፣ የተማሪዎችና የመምህራን ማደሪያ፣ ቤተ-ሙከራ ፣ ዲጂታል ዘመናዊ ቤተ መጽሐፍት ፣ ካፍቴሪያ ፣ የቢሮ አገልግሎት ፣ ዘመናዊ ጅምናዚየም ፣ የመዋኛ ገንዳ ፣ አንፊ ቴአትር ፣ የመዝናኛ ማዕከል ፣ የልብስ ማጠቢያ ገንዳዎችን ጨምሮ የተለያዩ አገልግሎት መስጫዎችን ያካተተ ነው።
ግንባታውን ከአንድ ዓመት ባነሰ ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ እንደሚሰራ መገለጹን ከዞኑ ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል ።