የሀገር ውስጥ ዜና

የህዝብና የመንግስት ሀብት ምዝበራን ለማጋለጥ ሚዲያው የሚጫወተው ሚና ግልጽነትን ለመፍጠር ያስችላል – ምሁራን

By Meseret Awoke

March 03, 2022

አዲስ አበባ፣ የካቲት 24፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ የህዝብና የመንግስት ሀብት ምዝበራን ለማጋለጥ ሚዲያው በምርመራ ዘገባዎች የሚጫወተው ሚና በመንግስት አስተዳደር ግልጽነትን ለመፍጠር እንደሚያስችል የጸረ ሙስና አንቂና የጋዜጠኝነት ምሁራን ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሚዲያው ሙሰኞችን ለማጋለጥ ምርመራዎችን እንዲሰራ ይደረጋል ማለታቸው የሚታወስ ነው።

የጸረ ሙስና አንቂና የህግ ባለሙያ አቶ ክብረአብ አበራ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደተናገሩት፥ መገናኛ ብዙሃኑ ሚናቸውን መጫወት ሲጀምሩ ውስብስብና ስልጣንን ተገን አድርገው ስርቆት የሚፈጽሙ ባለስልጣናትን ጭምር በምርመራ ማጋለጥ ይቻላል።

ይህ እንዲሆን ግን ለሚዲያ ባለሙያው ደህንነቱ የተጠበቀ ከባቢን መፍጠርና የሚዲያ ተቋማቱ ከተለምዷዊ አሰራራቸው ወደ ጠያቂነት መሸጋገር ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

በዲላ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና የኮሙኒኬሽን መምህር አቶ አያሌው ደጀን በበኩላቸው፥ የሙያ መርህን ጠብቆ በመስራት ውስብስብ የሆኑ የስርቆት ድርጊቶችን ማጋለጥ የሚጠበቅባቸው ሚዲያዎች የልማት አደናቃፊ ድርጊቶችን ይፋ በማውጣት ሀላፊነታቸውን መወጣት ይችላሉ ነውያሉት።

በስልጣናቸው ዛቻና ማስፈራሪያ ለማድረግ የሚሞክሩ ሊያጋጥሙ እንደሚችሉ የሚጠቀሱት አቶ አያሌው ፥ ለውጤታማነቱ መንግስት ድጋፍ ማድረግ አለበት ብለዋል።

የምርመራ ጋዜጠኝነትን በሚሰሩ ባለሙያዎች ላይ የስም ማጥፋትና የፖለቲካ በቀል ሊፈጸምባቸው እንደሚችል የሌሎች ሀገራትን ልምድ ጠቅሰዋል ምሁራኑ።

ሚዲያዎች በሚሰሯቸው የስልጣን መባለግን የሚያጋልጡ የምርመራ ዘገባዎች በሀገራት ግልፅነትና ተጠያቂነት እንዲሰፍን ማድረግ ችለዋል ያሉት ምሁራኑ ፥ የዋተርጌት ቅሌትና የፓናማ ፔፐር የምርመራ ዘገባዎች ልምድን መውሰድ ይቻላል ብለዋል ።

በሀይለየሱስ መኮንን

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!