ስፓርት

የኢትዮጵያ የማራቶን ዱላ ቅብብል ውድድር በሶማሌ ክልል ይካሄዳል

By ዮሐንስ ደርበው

April 08, 2022

 

አዲስ አበባ፣መጋቢት 30፣ 2014(ኤፍ ቢ ሲ) 17ኛው የኢትዮጵያ የማራቶን ዱላ ቅብብል ውድድር ሚያዚያ 9 ቀን 2014 ዓ.ም በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማ ይካሄዳል።

በውድድሩ ላይ ክልሎች፣ ከተማ አስተዳደሮች፣ ክለቦች፣ የአትሌቲክስ ማሰልጠኛ ማዕከላትና ተቋማት እንደሚሳተፉ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።

የውድድሩ አላማ ለክልሎች፣ ከተማ አስተዳደሮችና ክለቦች የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር እድል መፍጠርና ተተኪ አትሌቶችን ማፍራት እንደሆነ ተገልጿል።

የማራቶን ዱላ ቅብብል ውድድሩ በሴትና ወንድ ድብልቅ እንደሚካሄድና በአንድ ቡድን ሶስት ተወዳዳሪ ከአንድ ተጣባባቂ ማስመዝገብ እንደሚቻል ፌዴሬሽኑ አመልክቷል።

በውድድሩ ላይ ለመሳተፍ ከመጋቢት 15 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ምዝገባ እየተካሄደ እንደሚገኝና ሚያዚያ 4 ቀን 2014 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅም ነው የተገለጸው።

በውድድሩ የሚሳተፍ አትሌት፣ አሠልጣኝ፣ ቡድን መሪና ሌሎች የልዑካን ቡድን አባላት ከሚኖሩበት አካባቢ የኮቪድ-19 ምርመራ ውጤት ማቅረብ ይጠበቅባቸዋልም ነው የጠባለው፡፡

በቡድን ከ1 እስከ 3 ለሚወጡ አትሌቶች የሜዳሊያና የገንዘብ ሽልማት እንዲሁም በቡድን አሸናፊ ለሚሆኑ ክልሎች፣ ከተማ አስተዳደሮችና ክለቦች የዋንጫ ሽልማት ያገኛሉ ተብሏል።

የማራቶን ዱላ ቅብብሉ በ6 የኪሎ ሜትር ርቀቶች ተከፋፍሎ እንደሚከናወን ኢዜአ ዘግቧል።

ከዱላ ቅብብሉ በተጨማሪ የ10 ኪሎ ሜትር ሕዝባዊ ሩጫ እንደሚካሄድም የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።