የሀገር ውስጥ ዜና

በኢትየጵያ ላይ ማዕቀብ መጣል ማለት የቀጠናውን ፀረ- ሰላም ኃይሎች የሚያጠናክር ነው- የደቡብ ሱዳን ሚኒስትር

By Meseret Awoke

April 16, 2022

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 8፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትየጵያ ላይ ማዕቀብ መጣል ማለት የክፍለ አህጉሩን ፀረ- ሰላም ኃይሎችን የሚያጠናክርና በቀጠናው አለመረጋጋት እንዲሰፍን የሚያደርግ ነው ሲሉ የደቡብ ሱዳን የፐብሊክ ሰርቪስ እና የሰው ሀብት ልማት ሚኒስትር ተናገሩ፡፡

በደቡብ ሱዳን የኢፌዲሪ አምባሳደር ነቢል መኽዲ ከደቡብ ሱዳን የፐብሊክ ሰርቪስ እና የሰው ሀብት ልማት ሚኒስትር ባንጋሲ ጆሴፍ ባኮሶሮ ጋር ተወያይተዋል።

በሁለቱም ወገኖች የተደረገው ውይይት በዋናነት የሁለቱን ሀገራት ወቅታዊ ጉዳዮች የዳሰሰ ነው ተብሏል።

የደቡብ ሱዳን የፐብሊክ ሰርቪስ እና የሰው ሀብት ልማት ሚኒስትር ባንጋሲ ጆሴፍ ባኮሶሮ በዚህ ወቅት ፥ የኢትዮጵያ መንግስት ለትግራይ ክልል የሚደረጉ ሰብዓዊ ድጋፎችን ለማመቻቸት ላደረገው ቁርጠኝነት አድናቆታቸውን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያን ስም ለማጠልሸት አንዳንድ የውጭ አካላት የሚያካሂዱትን የፕሮፓጋንዳ ዘመቻም ሚኒስትሩ አውግዘዋል።

አክለውም በኢትዮጵያ ላይ የሚጣለው ማዕቀብ ፀረ-ሰላም ኃይሎችን የሚያበረታታ ከመሆኑም በላይ በቀጠናው አለመረጋጋት እንዲሰፍን ያደርጋል ብለዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት ለደቡብ ሱዳን የህዝብ አገልጋዮች በአቅም ግንባታ እና በሰው ሃይል ልማት ላይ የሚያደርገውን ድጋፍ አድናቆታቸውን ገልጸዋል።

በሲቪል ሰርቪስ ዘርፍ ያለውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማጠናከር መስማማታቸውንም ከውጭ ጉዳይ ሚነስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ!

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!