የሀገር ውስጥ ዜና

የጃፓን ኩባንያዎች በኢትዮጵያ መዋዕለ-ንዋያቸውን ማፍሰስ እንደሚፈልጉ አስታወቁ

By Alemayehu Geremew

April 23, 2022

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 15፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የጃፓን ባለሐብቶች በኢትዮጵያ ባሉ ክፍት የኢንቨስትመንት አማራጮች ላይ በቂ ግንዛቤ እንዳገኙና መዋዕለ-ንዋያቸውን ማፍሰስ እንደሚፈልጉ አስታወቁ፡፡

በጃፓን የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ “ኢንስፓየር አፍሪካ” ከተሰኘ ማኅበር ጋር በመተባበር የጃፓን ባለሐብቶች በኢትዮጵያ መዋዕለ-ንዋያቸውን እንዲያፈሱ የሚጋብዝ ሴሚናር አካሂዷል፡፡

በሴሚናሩም በጃፓን ውስጥ የሚገኙ በውሃ ልማት፣ በግንባታ፣ በመድሐኒት ኢንዱስትሪ፣ በኤሌክትሮኒክስ፣ እና ቴክኖሎጂ የተሰማሩ የስድስት ኩባንያዎች፣ ባለሐብቶች እና አመራሮች ተሳትፈዋል፡፡

የጃፓን ባለሐብቶች በኢትዮጵያ መዋዕለ-ንዋያቸውን ቢያፈሱ አዋጭ የሆኑ የስራ መስኮች፣ በኢትዮጵያ የንግድ ህግ መሰረት በንግድ፣ ጨርቃጨርቅ፣ መድሐኒት፣ ማዕድን፣ አይ.ሲ.ቲ እና በሌሎች የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ በተለይም የግብርና ምርቶችን ማቀነባበር ላይ ቢሰማሩ የሚያገኟቸው ልዩ ጥቅሞች ተዘርዝረው ቀርበዋል፡፡

በጃፓን የሚገኘውን የኢትዮጵያ ኤምባሲ በመወከልም አቶ ዮሐንስ ፋንታ፥ የሁለቱን ሀገራት ታሪካዊ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያነሱ ሲሆን፥ በቀጣይም የሀገራቱን ግንኙነት በኢንቨስትመንቱ ዘርፍ፣ ንግድ እና ቴክኖሎጂ ሽግግር ይበልጥ በማስተሳሰር ማስፋት እንደሚገባ መልዕክት ማስተላለፋቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡