የሀገር ውስጥ ዜና

የኩፍኝ፣ ፖሊዮና ቢጫ ወባ ወረርሽኝን ለመከላከል ያለመ የክትባት ሣምንት ሊካሄድ ነው

By Feven Bishaw

April 28, 2022

 

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 20፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኩፍኝ፣ ፖሊዮና ቢጫ ወባ ወረርሽኝን ለመከላከል ያለመ የክትባት ሣምንት ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ ሊካሄድ መሆኑን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ድጉማ በሰጡት መግለጫ ÷ የአፍሪካ የክትባት ሣምንትን ምክንያት በማድረግ የሚከናወነው የክትባት ዘመቻው በተለይም በጸጥታ ችግር ምክንያት ክትባት ባልተሰጠባቸው ቦታዎች ይሰጣል ብለዋል፡፡

የክትባት ሣምንቱ ማህበረሰቡ በክትባት ጠቀሜታ ላይ ትክክለኛውን ግንዛቤ እንዲጨብጥ ለማድረግና የክትባት ተደራሽነትን ለማስፋት መሆኑንም አመላክተዋል፡፡

የክትባት ዘመቻው ዓላማ÷ በወረርሽኝ ደረጃ ሊነሱ ይችላሉ ተብሎ የተሰጉትን ኩፍኝ፣ ፖሊዮ እና ቢጫ ወባን ለመከላከል መሆኑን የጠቆሙት ዶክተር ደረጄ÷ ይህም ተፈናቃይ ዜጎች ባሉባቸው አካባቢዎች በስፋት የሚሰጥ ይሆናል ብለዋል፡፡

ከወረርሽኝ መከላከል ባለፈ ለሕጻናት የአንጀት ተወሃሲያን መከላከያ፣ ቫይታሚን ኤ እና በምግብ እጥረት የተጎዱ ሕጻናትን በመለየት ሕክምና እንደሚሰጥ መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡