የሀገር ውስጥ ዜና

የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን በዩኔስኮ ለማስመዝግብ እየተሰሩ ባሉ ስራዎች ላይ ውይይት ተካሄደ

By Melaku Gedif

May 03, 2022

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ25፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) ለማስመዝግብ እየተሰሩ ባሉ ስራዎች ዙሪያ ውይይት ተደርጓል፡፡

በውይይቱ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳን ጨምሮ  የቱሪዝም ሚኒስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ፣የኢትዮጵያ ዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን እና የኦሮሚያ ቱሪዝም ቢሮ አመራሮች፣ በኢትዮጵያ የፍራንክፈርት  የሥነ እንስሳት ባለሙያዎች ማህበር ዳይሬክተር እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡

ባለድርሻ አካላቱ በቀጣይ ብሔራዊ ፓርኩ በዩኔስኮ ተመዝግቦ ኢትዮጵያ ከዘርፉ ተጠቃሚ በምትሆንበት ሂደት ዙሪያ እየተሠሩ ባሉ ስራዎች ላይ መክረዋል፡፡

በፓርኩ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ እና ማህበረሰቡ ብሔራዊ ፓርኩን በመጠበቅ  ከፓርኩ ተጠቃሚ የሚሆንበት አሰራር እንደሚዘረጋ መገለጹንም ከኦሮሚያ ቱሪዝም ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡