የሀገር ውስጥ ዜና

የህዳሴ ግድብን በስጦታ ወይም በሌላ ወገን ይሁንታ የምንገነባው አለመሆኑ ሊታወቅ ይገባል-መንግስት

By Tibebu Kebede

March 03, 2020

አዲስ አበባ፣ የካቲት 24፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብን የምትገነባው ግድብ የመገንባት ሙሉ መብት ስላላት መሆኑን አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ገለፁ።

የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው እና የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል።

 

በህዳሴ ግድብ ላይ እየተካሄደ ካለው ድርድር ጋር ተያይዞ ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ፥ ከውሃ ሙሌትና አለቃቅ ጋር ተያይዞ ተገቢ ያልሆኑ የህግ ማዕቀፎች እንዲቀርቡ አንፈልግም ሲሉም ተናግረዋል።

ከግድቡ ውሃ ሙሌት ጋር ተያይዞ በግልፅ የተቀመጠ ነው፤ ከዚያ ውስጥ ድርቅ ሲከሰት የሚለው ነው የሚያከራክረው፤ ይህ እስኪፈታ ጊዜ ይጠይቃል ነው ያሉት ሚኒስቴሩ።

የምንፈርመው ስምምነት ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፤ ከህዝብ ጋር፣ ከሚመለከታቸው የዘርፉ ተቋማት ጋር በቂ ውይይት አድርገን ነው መፈረም ያለብን ያሉት ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ፥ ከዚህ በዘለለ ግን ብቁ ያልሆነ ሰነድ ሲቀርብ አንፈርምም ብለዋል።

ከአሜሪካ ሚና ጋር በተያያዘም ኢትዮጵያ በመጀመሪያው የቴክኒክ ስብሰባ ላይ አደራዳሪም ሆነ አመቻች እንደማትፈልግ በግልፅ አስቀምጣ የነበረ ቢሆንም፥ በአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጥያቄ መሰረት በታዛቢነት እንዲገቡ መደረጉንም ነው ያነሱት።

በአራቱ የቴክኒክ ስብሰባዎች ላይም አሜሪካ በዚሁ ሚናዋ ነበር የቀጠለችውም ብለዋል ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ።