Fana: At a Speed of Life!

የአውሮፓ ኅብረት ኩባንያዎች ከሩሲያ ጋዝ መግዛታቸውን እንዲቀጥሉ በቀረበው ዕቅድ ላይ ተስማማ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 8፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የአውሮፓ ኅብረት በሩሲያ ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን በማይጻረር መልኩ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ከሩሲያ ጋዝ መግዛታቸውን እንዲቀጥሉ በቀረበው ዕቅድ ላይ ተስማማ፡፡

የአውሮፓ ኅብረት ባለሥልጣናት በደረሱት አዲስ ሥምምነት መሠረት፥ ኩባንያዎች ከሩሲያ ለሚገዙት ጋዝ ክፍያውን አዲስ በወጣው ዝርዝር መመሪያ መሠረት በዶላርና በዩሮ ቀድመው መፈጸም ይጠበቅባቸዋል ተብሏል፡፡

በርካታ ዓለም አቀፋዊ ኩባንያዎች በተቀመጠላቸው ጊዜ መሠረት አስፈላጊውን መሥፈርት አሟልተው ክፍያቸውን በዚህ ወር እንዲያጠናቅቁ ሩሲያ አስጠንቅቃለች፡፡

ይህ ካልሆነ ግን ባለፈው ወር ቡልጋሪያ እና ፖላንድ ላይ እንዳደረኩት ሁሉ አቅርቦት የማቋርጥ ይሆናልም ነው ያለችው ሩሲያ፡፡

አዲሱ ሥምምነት የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሜር ፑቲን ባሳለፍነው መጋቢት ወር ላይ “አጋሮቼ አይደሉም” ባሏቸው ሀገራት ላይ ያሳለፉትን ” ጋዝ መግዛት የሚፈልጉ ሀገራት በጋዝፕሮም ባንክ በኩል የዶላርና የዩሮ አካውንት ከፍተው ክፍያ መፈጸም ይጠበቅባቸዋል” የሚለውን አስገዳጅ መመሪያ አይጥስም ነው የተባለው፡፡

ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ፊንላንድ ከአሁኑ የሩሲያን አቋም እየተቃወመች እንደምትገኝ አር ቲ ኒውስ ዘግቧል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.