የዜጎች ሰላም፣ ደህንነትና የሀገር ቀጣይነት የሚረጋገጠው የህግ የበላይነት ሲከበር ብቻ ነው፡፡ በመላ ኢትዮጰያ የሚገኘው ዜጋ በሰላም ወጥቶ የመግባት መብቱ እንዲከበርና ደህንነቱ እንዲጠበቅ የህግ የበላይነትን ማስፈን ደግሞ ህዝብ ለመንግስት የሰጠው ሃላፊነት ነው። የዜጎች ነፃነትና ዲሞክራሲም መስፈን የሚችለዉ የትኛውም ጉልበት አለኝ የሚል አካል ከህግ በታች መሆኑ እስከተረጋገጠ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ነፃነትንና መብትን ከለላ በማድረግ የሚፈፀም የትኛውም አይነት እኩይ ተግባርን መንግስት አይታገስም፡፡ መንግስት በሆደ ሰፊነት በተደጋጋሚ ጊዜ የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ከቁብ ያልቆጠሩ ኃይሎችን መግታት የሚቻለው የህግ የበላይትን በማስከበር ብቻ ነው፡፡ ሁሉም ዜጋና የተለየ አመለካከት ያላቸው ወገኖችም መብትና ጥቅሞቻቸዉን ማስከበር የሚችሉት የህግ የበላይነት ሲረጋገጥና ሰላም ሲሰፍን ብቻ ነው፡፡