የሚኒስትሮች ምክር ቤት የ2015 የፌዴራል መንግስት ረቂቅ በጀት 786 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር እንዲሆን ውሳኔ አሳለፈ
አዲስ አበባ፣ግንቦት 26፣2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የሚኒስትሮች ምክር ቤት የ2015 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግስት ረቂቅ በጀት 786 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር እንዲሆን ውሳኔ አሳለፈ።
የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 9ኛ መደበኛ ስብሰባ በ2015 የፌዴራል መንግስት ረቂቅ በጀት ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል፡፡
የፌዴራል መንግስት የ2015 በጀት ዓመት የበጀት ዝግጅት በአስር ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ የተቀመጡ ግቦችን ከማስፈጸም አኳያ፣ የሀገር ደህንነትን ከማስጠበቅ፣ የተፈናቀሉ ዜጎችን ከመርዳትና የወደሙ መሰረተ ልማቶችን እና አገልግሎቶችን መልሶ ከማቋቋም፣ ቀጣይ የማህበራዊና የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን አቅጣጫዎችና ዓላማዎችን ማሳካት ማእከል በማድረግ እንዲሁም፥ የ2015-2019 የመካከለኛ ዘመን የማክሮ ኢኮኖሚና የፊስካል ማዕቀፉን መሰረት በማድረግ ተዘጋጅቶ የቀረበ መሆኑን ተመልክቷል።
በዚህም መሰረት ለ2015 በጀት ዓመት ለመደበኛ ወጪ ብር 347 ነጥብ 12 ቢሊየን፣ ለካፒታል ወጪ ብር 218 ነጥብ 11 ቢሊየን እንዲሁም ለክልል መንግሥታት ድጋፍ ብር 209 ነጥብ 38 ቢሊየን እና ለዘላቂ የልማት ግቦች ማስፈጸሚያ ብር 12 ቢሊዮን የተያዘ ሲሆን፥ አጠቃላይ የፌዴራል መንግሥት የ2015 ረቂቅ በጀት 786 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር ሆኖ ቀርቧል፡፡
ከ2014 በጀት ዓመት በጀት ጋር ሲነጻጸር የብር 111 ነጥብ 94 ቢሊዮን ወይም የ16 ነጥብ 59 በመቶ እድገት አሳይቷል፡፡
ምክር ቤቱም በቀረበለት የፌዴራል መንግሥት የ2015 ረቂቅ በጀት ላይ በስፋት ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል ይጸድቅ ዘንድ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡