የሀገር ውስጥ ዜና

15 ሽጉጥ በተሽከርካሪ ደብቆ ሲንቀሳቀስ የነበረ ግለሰብ ከግብረ አበሩ ጋር በቀጥጥር ሥር ዋሉ

By Alemayehu Geremew

June 30, 2022

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 23፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ፖሊስ እና የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት በጋራ ባደረጉት ክትትል 15 ሽጉጥ በተሽከርካሪ ውስጥ ደብቆ ሲንቀሳቀስ የነበረ ግለሰብ ከግብረ-አበሩ ጋር በቁጥጥር ስር መዋላቸውን አስታውቀዋል፡፡

ግለሰቡ የጦር መሣሪያውን ይዞ የተገኘው በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ልዩ ቦታው አዲሱ ገበያ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡

ፖሊስ ባደረገው ምርመራ በዚህ የወንጀል ድርጊት ተሳትፎ ያለውን አንድ ሌላ ግለሰብም በመያዝ ምርመራው መቀጠሉም ነው የተገለጸው፡፡

የጦር መሣሪያ አዘዋዋሪዎች ልዩ ልዩ ሥልቶችን በመጠቀም የኅብረተሰቡን ሠላምና ደኅንነት ሥጋት ውስጥ ለመጣል እየሠሩ መሆናቸውንም የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውሷል፡፡

ፖሊስ ኅብረተሰቡ የከተማዋን ሠላምና ደኅንነት ለማደፍረስ የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦችን ህገ-ወጥ ተግባር በማጋለጥ ለፀጥታ አካላት እያሳወቁ መሆኑን ገልጾ ትብብራቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጥሪውን አስተላልፏል፡፡