ዓለምአቀፋዊ ዜና

ሩሲያ አርክቲክ አካባቢ ከፍተኛ የነዳጅ ክምችት ማግኘቷን አስታወቀች

By Alemayehu Geremew

July 04, 2022

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 27፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ሩሲያ በአርክቲክ አካባቢ በሚገኘው ፔቾራ ባሕር 82 ሚሊየን ቶን የሚገመት የነዳጅ ዘይት ክምችት ማግኘቷን አስታወቀች፡፡

ነዳጁን ያገኘው በሩሲያ መዲና ሞስኮ መቀመጫውን ያደረገው “ሮስኔፍት” የተሰኘ የሀገሪቷ የነዳጅ ኩባንያ መሆኑን አር ቲ ዘግቧል፡፡

ኩባንያው ነዳጅ ባወጣበት በመጀመሪያው የሙከራ ጊዜ በቀን 220 ኪዩቢክ ሜትር ያህል ነዳጅ ማግኘቱን በመግለጫው አስታውቋል፡፡

“ሮስኔፍት የነዳጅ ኩባንያ” በፔቾራ የተካሄደው አሰሳ በአካባቢው ከፍተኛ የነዳጅ ዘይት አቅም መኖሩን እንደሚያመላክት እና በአካባቢው ተጨማሪ ጥናትና ምርምር ለማድረግ እንዳነሳሳው ገልጿል።

ኩባንያው በአርክቲክ አካባቢ የነዳጅ አሰሳ ለማካሄድ በአጠቃላይ 28 ያህል የባሕር ዳርቻ ፈቃዶች ያሉት ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ ስምንት ያህሉ ፈቃዶቹ በፔቾራ ባሕር ላይ አሰሳ እንዲያደርግ የተፈቀዱለት ናቸው ተብሏል፡፡