የአሜሪካ ኮንግረስ አባላት ለጉብኝት ታይዋን ገቡ
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 8፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በዛሬው ዕለት የአሜሪካ ኮንግረስ ልዑካን ቡድን ለሁለት ቀናት ጉብኝት ታይዋን መግባታቸው ተገለጸ።
የአሜሪካ ኮንግረስ ሕግ አውጪ አባላት ታይዋን የገቡት፥ የአሜሬካ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ናንሲ ፔሎሲ ታይዋንን ከጎበኙ ሁለት ሣምንታት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡
በታይዋን ዋና ከተማ ታይፔይ የሚደረገውን የልዑካኑን ጉብኝት ይፋ ያደረገው ደሴቲቱን እንደ ራስ-ገዝ አስተዳደር ቆጥሮ እንደ አሜሪካ ኤምባሲ የሚንቀሳቀስ ተቋም ነው ተብሏል፡፡
እንደ ተቋሙ መረጃ ዴሞክራቱ የማሳቹሴትስ ሴናተር ኤድ ማርኬይ ልዑካን ቡድኑን መርተው ታይዋን ገብተዋል።
በጉብኝቱ የዴሞክራቶቹ ተወካይ የሆኑት ÷ ጆን ጋራሜንዲ እና አለን ሎዌንታል ከካሊፎርኒያ እንዲሁም ዶን ቤየር ከቨርጂኒያ ከቡድን መሪው ጋር በታይፔይ ተገኝተዋልም ነው የተባለው፡፡
በተጨማሪ ከሪፐብሊካኑ ወገን ደግሞ አሙአ አማታ ኮልማን ራዴዋገን ከሳሞአ በመርሐ-ግብሩ ላይ ተሳታፊ መሆናቸውን አር ቲ ዘግቧል፡፡
ልዑካን ቡድኑ ከታይዋን መሪዎች ጋር በቀጣይ በሚኖራቸው ግንኙነት ዙሪያ እንደሚመክሩ ኢንስቲቲዩቱ ገልጿል።
በቀጠናዊ ደኅንነት፣ በንግድ እና ኢንቨስትመንት፣ በዓለምአቀፍ የአቅርቦት ሰንሰለቶች፣ በዓየር ንብረት ለውጥ እና ሌሎች ጉዳዮች ላይ እንደሚወያዩም ነው የተመለከተው፡፡