የሀገር ውስጥ ዜና

አምባሳደር ስለሺ በቀለ ከአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ ጋር ተወያዩ

By Alemayehu Geremew

August 17, 2022

አዲስ አበባ ፣ ነሐሴ 11 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ስለሺ በቀለ ከአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ ማይክል ሐመር ጋር ተወያዩ።

በዚህ ወቅትም በኢትዮጵያ ከዘላቂ ሰላም ግንባታ፣ ሰብአዊ ድጋፍ አቅርቦት፣ ተጠያቂነትንና ዴሞክራሲን ከማስፈን፣ ብሄራዊ ውይይት እና ከታላቁ ህዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ ሃሳብ ተለዋውጠዋል።

በውይይታቸው ወቅት በተነሱ ጉዳዮች ዙሪያ ባሉ መሻሻሎች እና ባጋጠሙ ተግዳሮቶች ዙሪያ ሃሳብ መለዋወጣቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል።

አምባሰደር ስለሺ በውይይታቸው ልዩ መልዕክተኛው ከኢትዮጵያ የስራ ሃላፊዎች ጋር ላላቸው ግንኙነት እና የቆየውን የሀገራቱን ግንኙነት ለማጠናከር ላደረጉት ጥረት አድናቆታቸውን ገልጸዋል።

ልዩ መልዕክተኛው በበኩላቸው በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታ ባዩት አበረታች ለውጥ መደሰታቸውን ለአምባሳደር ስለሺ ገልጸውላቸዋል።