የሀገር ውስጥ ዜና

ጤና ሚኒስቴር ለ100 ሺህ ዜጎች ነጻ የሕክምና አገልግሎት ሊሰጥ ነው

By Alemayehu Geremew

August 19, 2022

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 13፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ጤና ሚኒስቴር 100ሺህ ለሚሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች ነጻ የጤና ምርመራና የሕክምና አገልግሎት ለመስጠት መዘጋጀቱን አስታወቀ።

የጤና ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ ዛሬ በሰጡት መግለጫ÷የሕክምና አገልግሎቱ “በጎነት ለጤናችን ” በሚል መሪ ቃል ከነሐሴ 16 እስከ 21 ቀን 2014 ለተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በበጎ ፈቃደኛ የጤና ባለሙያዎች የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ለሥድስት ተከታታይ ቀናት በሚቆየው የበጎ ፈቃድ ሥራ አቅመ ደካማ ለሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎችና ለጎዳና ተዳዳሪዎች የተለያዩ የሕክምና አገልግሎት እንደሚሰጣቸው ጠቁመዋል።

ከሚሰጡ የጤና ምርመራዎች መካከል የስኳር ሕመም ፣ የደም ግፊት፣ የዐይን ሕመም ሕክምና እንዲሁም ሌሎች ተላላፊ እና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ይገኙበታል ተብሏል።

ተላላፊ እና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን አስመልክቶ ለኅብረተሰቡ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ እንደሚከናወንም ዶክተር ሊያ መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።