Fana: At a Speed of Life!

የጣሊያኗ ሰርዲኒያ ለአዳዲስ ነዋሪዎቿ 15 ሺህ ዩሮ ልትከፍል ነው

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 18፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ውብ ደሴት ወደ ሆነችው ሰርዲኒያ ተዛውሮ መኖር ለሚፈልግ ጣሊያናዊ ነዋሪ 15 ሺህ ዩሮ ክፍያ እንደሚያገኝ የሀገሪቷ መንግስት አስታወቀ፡፡

የጣሊያን መንግስት የማበረታቻ ውሳኔውን ያሳለፈው በርካታ ወጣቶች ለሥራ ፍለጋ በሚል ሰበብ ደሴቲቱን ለቀው ወደ ትላልቅ ከተሞች በሚያደርጉት ፍልሰት የነዋሪዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በመቀነሱ ነው ተብሏል፡፡

ይህን ተከትሎም የአካባቢው ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ መዳከሙ ነው የተነገረው፡፡

ደሴቷ ከ1 ሺህ 609 ኪሎ ሜትር በላይ አሸዋማ የባሕር ዳርቻዎች፣ ውብ የወደብ ከተሞች እና ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ1 ሺህ 500 ክፍለ ዘመን በፊት የተገነቡ የነሐስ ዘመን ኅንጻዎች ፍርስራሾች የሚገኙባት ውብ ታሪካዊ ሥፍራ መሆኗም ተመላክቷል፡፡

ሰርዲኒያ በሜዲትራኒያን ባሕር ሁለተኛዋ ትልቋ ደሴት መሆኗንም ዴይሌ ሜይል ዘግቧል፡፡

የጣሊያን ባለሥልጣናት ዜጎች ወደ ሀገሪቷ ገጠራማ አካባቢዎች ሄደው እንዲኖሩ ለማሳመን እና በትናንሽ ከተሞች ውስጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለማበረታታት ከ45 ሚሊየን ዩሮ በላይ መድበዋል ነው የተባለው።

ይህ ገንዘብ ወደ ገጠራማ የሀገሪቱ ትናንሽ ከተሞች በመዛወር ቤት በመግዛት መኖር ለሚፈልጉ ነዋሪዎች የተመቻቸ ብድርና ድጋፍ መሆኑም ነው የተገለጸው።

ድጋፉም አዳዲስ ነዋሪዎቹ ጥንታዊና ያረጁ ቤቶችን ገዝተው በማስዋብና በማደስ እንዲኖሩባቸው ብሎም በአካባቢዎቹ ለሚጀምሯቸው የንግድ እንቅስቃሴዎች ለሚያስፈልጋቸው ወጪ የሚውል ይሆናል።

ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.