የሀገር ውስጥ ዜና

ከተማ አስተዳደሩ በጥበበኛ እጆች የሚሰሩ የዕደ-ጥበብ ስራዎችን ያበረታታል – ከንቲባ አዳነች አቤቤ

By Shambel Mihret

September 07, 2022

አዲስ አበባ፣ ጳጉሜን 2፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በጥበበኛ እጆች የሚሰሩ መሰል የዕደ-ጥበብ ስራዎችን ያበረታታል፣ ድጋፍ ያደርጋልም ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤን ጨምሮ የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች አምራቾችንና አምራችነትን ለማበረታታት የ”ሙያ ኢትዮጵያ” ሀላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበርን ጎብኝተዋል፡፡

የሸክላ እና የሽመና ውጤቶችን ወደ ውጭ ሀገር የሚልከው ሙያ ኢትዮጵያ÷ ለበርካታ የዕደ-ጥበብ ባለሙያዎች የስራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ የውጭ ምንዛሬ ለኢትዮጵያ ማስገኘት የቻለ ማህበር መሆኑን ከከንቲባ ጽህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡

የሙያ ኢትዮጵያ ባለቤት ስራ አስኪያጅና ዲዛይነር ወይዘሮ ሳራ አበራ በበኩላቸው÷ለጥበበኞች ልዩ ስልጠና በመስጠት የስራ ዕድል በመፍጠሬ ከማገኘው ገቢ የበለጠ ደስተኛ ነኝ ብለዋል፡፡