የሀገር ውስጥ ዜና

አሸባሪው ህወሓት ሰርጎ በገባባቸው አካባቢዎች ንጹሃንን በግፍ እየገደለ መሆኑን ነዋሪዎች ተናገሩ

By Alemayehu Geremew

September 17, 2022

አዲስ አበባ ፣ መስከረም 7 ፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የአሸባሪው የህወሓት ታጣቂ ቡድን እየሰረገ በገባባቸው የሰሜን ወሎ አካባቢዎች ንጹሃንን በግፍ እየገደለ መሆኑን ነዋሪዎች ተናገሩ።

ከቆቦ ወረዳ ወርቄ ቀበሌ አሸባሪው ህወሓት በከፈተው ጦርነት ምክንያት ተፈናቅለው በሰሜን ወሎ ዞን መርሳ ከተማ የሚገኙ ተፈናቃዮች ታጣቂ ቡድኑ ንጹሃንን በግፍ እየገደለ መሆኑን ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል።

ነዋሪዎቹ እንደሚሉት የሽብር ቡድኑ አካባቢያቸውን እንዲለቁ ከማድረጉም በላይ የአርሶ አደሮችን ቤት እና ንብረት በማቃጠሉ ለሰቆቃ ተዳርገዋል።

በቆቦ ወረዳ የወርቄ ቀበሌ ነዋሪዎች ከዚህ በፊት አሸባሪው ህወሓት የከፈተውን ጦርነት በመመከት አካባቢያቸውን አስከብረው ነበር።

ይሁን እንጅ አሸባሪው ታጣቂ አሁን በከፈተው ጦርነት የአካባቢውን ነዋሪዎች ለመበቀል መምጣቱን ገልጸዋል።

ነዋሪዎቹ አካባቢውን ለቀው ከወጡ በኋላም ንብረቶቻቸውን እየዘረፈና ቤታቸውን እያቃጠለ ንጹሃንን እየገደለ መሆኑንም ነው የሚናገሩት።

ቀያቸውን ጥለው የተጠጉበት የመርሳ ከተማ እና የአካባቢው ሕዝብ እያደረገላቸው ላለው ድጋፍ እና ወገናዊ አጋርነት አመስግነዋል።

በለይኩን ዓለም