የሀገር ውስጥ ዜና

በኦሮሚያ ክልል በኮሮና ቫይረስ የተፈጠረውን ወቅታዊ ሁኔታ ተከትሎ ያለአግባብ በሸቀጦች ላይ ዋጋ የጨመሩ 1 ሺህ 85 ድርጅቶች ታሸጉ

By Tibebu Kebede

March 20, 2020

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 11፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ)  በኢትዮጵያ በኮሮና ቫይረስ የተፈጠረውን ወቅታዊ ሁኔታ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል ያለአግባብ በሸቀጦች እና አገልግሎቶች ላይ ዋጋ የጨመሩ 1 ሺህ 85 ድርጅቶች ታሸጉ።

የክልሉ የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌታቸው ባልቻ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደተናገሩት፥ ከዚህ ህገወጥ ድርጊት ጋር በተያያዘ 13 ግለሰቦችም ለህግ ቀርበዋል።

ይህ በህገወጦች ላይ የሚደረገው ክትትልም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው አቶ ጌታቸው ያስታወቁት።

ነጋዴው ህብረተሰብ በዚህ ወቅት በያገባኛል፣ በእኔነት እና ከማንኛውም ግዜ በበለጠ በሀገራዊ ስሜት ከሸማቹ ህዝብ ጎን እንዲቆምም ነው ያሳሰቡት።