የሀገር ውስጥ ዜና

ሁዋጃን ኢንተርናሽናል የኮሮናቫይስ ወረርሽኝ መከላከያ ግብዓቶችን ለኢትዮጵያ ለገሰ

By Tibebu Kebede

March 21, 2020

አዲስ አበባ ፣ መጋቢት 12 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ)  ሁዋጃን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ  የኮሮናቫይስ ወረርሽኝ መከላከያ ግብዓቶችን ለኢትዮጵያ ለገሰ።

ድርጅቱ ኢትዮጵያ የቫይረሱን ወረርሽኝ ለመከላከል የምታደርገውን ጥረት ለማገዝ ግብአቶችን በመለገሱም የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ምስጋና አቅርበዋል።

ግብአቶቹም ፊትለፊት ሆነው ቫይረሱን ለመጋፈጥ ዝግጁ ለሆኑት የጤና ባለሙያዎች የሚሰራጩ ይሆናል ብለዋል።

“የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት በምንረባረብበት በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ ከአጋሮቿ ተመሳሳይ ድጋፍ ያስፈልጋታል”  ብለዋል።

የመጀመሪያው ዙር በአሊባባ አማካኝነት በጃክ ማ ፋውንዴሽን የተበረከቱ የምርመራ ቁሶች፣ የአፍ መሸፈኛ ጭምብሎች እንዲሁም ቫይረሱን የተመለከቱ መመሪያዎችም ስብስብ ነገ ይደርሳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

እነዚህ ቁሳቁሶች በመላው ኢትዮጵያ እንዲሁም እንዲደርሳቸው ለታሰበላቸው የአፍሪካ ሀገራት ለማሰራጨት ቅድመ ዝግጅት እየተካሄደ  እንደሚገኝ በትናንትናው እለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ ማሳወቃቸው የታወሳል።