የሀገር ውስጥ ዜና

አሸባሪው የህወሓት ቡድን በትግራይ ህዝብ ስም እየነገደ ነው- በዲላ የሚኖሩ የትግራይ ተወላጆች

By Meseret Awoke

October 13, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 3፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) አሸባሪው የህወሓት ቡድን በትግራይ ህዝብ ስም እየነገደ ነው ሲሉ በዲላ ከተማ የሚኖሩ የትግራይ ተወላጆች ገለጹ፡፡

በከተማዋ የሚኖሩ የትግራይ ተወላጆች በወቅታዊ አገራዊ ጉዳይ ዙሪያ ውይይት አካሂደዋል።

የውይይቱ ተሳታፊ የሆኑ የትግራይ ተወላጆች ህወሓት በትግራይ ህዝብ ስም እየነገደ የስልጣን ጊዜውን ለማራዘም እንጂ ለህዝቡ አስቦ እንዳልሆነ በውይይታቸው አንስተዋል፡፡

አሸባሪው ህወሓት መንግስት ያቀረበውን የሰላም ጥሪ ወደ ጎን በመተው ለ3ኛ ጊዜ ጦርነት መክፈቱ እንዳሳዘናቸውም ተሳታፊዎቹ ገልጸዋል፡፡

የትግራይ ህዝብ ፍላጎት ሰላም፤ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር በሰላም መኖር ሆኖ ሳለ ክልሉን ለብቻው አፍኖ ለእኩይ ዓላማ ማዋል የህወሓት የከሰረ ፖሊቲካ ቁማር ነው ብለዋል ተሳታፊዎቹ፡፡

ድርጊቱን በመላ ዓለም የሚኖር የትግራይ ተወላጆችም ሆኑ ሌሎች ሊያወግዙት እንደሚገባም ነው ያመለከቱት።

መንግስት የትግራይ ህዝብ ጠላት የሆነውን አሸባሪው የህወሐት ቡድን ስርዓት ለማስያዝ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ እንደሚደግፉ በመግለፅ፥ ማንኛውም እኩይ ተግባር ላይ የተሰማራን አሸባሪ አካል ለህግ አሳልፎ መስጠት እንደሚገባ መናገራቸውን የጌዴኦ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ህዝብ ግንኙነት መረጃ ያመለክታል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!