የሀገር ውስጥ ዜና

ከ27 ሚሊየን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸው የቁም እንስሳቶች እና የኮንትሮባንድ እቃዎች ተያዙ

By Mikias Ayele

October 19, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 9፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በህገወጥ መንገድ ከሀገር ሊወጡ የነበሩ 20 ሚሊየን ብር ግምታዊ ዋጋ ያላቸው የቁም እንስሳቶች እና ከ7 ሚሊየን ብር በላይ የሚያወጡ የኮንትሮባንድ እቃዎች መያዙን የጉምሩክ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡

በጅግጅጋ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽህፈት ድንበር ላይ የተያዙት 427 የቁም እንስሳቶች እና እርጥብ ጫት፣ ሙዝ፣ ነዳጅ እና የጥራጥሬ እህሎች መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡

የኮንትሮባንድ እቃዎቹ የተያዙት በጉምሩክ ኮሚሽን አመራሮች እና ሰራተኞች እንዲሁም የፌደራል ፖሊስ አባላት ባደረጉት ጥረት እና ክትትል መሆኑን የኮሚሽኑ መረጃ ያመላክታል፡፡

የኮንትሮባንድ አፈጻጸም ስልቱ ተለዋዋጭ በመሆኑ ድርጊቱን ለመግታትና በሀገር ኢኮኖሚ የሚያሳድረውን አሉታዊ ተጽእኖ ለመከላከል ሁሉም ባላድርሻ አካላትና ህብረተሰቡ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል፡፡