በሕገ ወጥ የውጭ ሀገራት ገንዘብ ምንዛሪ በተሰማሩ አካላት ላይ በጥናት የተመሰረት እርምጃ ተወሰደ
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስና ከኦሮሚያ ፖሊስ ጋር በመቀናጀት በሕገወጥ የውጭ ሀገራት ገንዘብ ምንዛሪ በተሰማሩ ግለሰቦችና ድርጅቶቻቸው ላይ ጥናትን መሰረት ያደረገ እርምጃ መወሰዱን አስታውቋል፡፡
አገልግሎቱ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው÷ ባለፉት ሁለት ወራት በሕገወጥ የውጭ ሀገራት ገንዘቦች ምንዛሪ ዙሪያ ሰፊና ጥልቀት ያለው ጥናት ሲካሄድ ነበር፡፡
ችግሩ በጥናት ከተለየ በኋላም መረጃዎችንና ማስረጃዎችን መነሻ በማድረግ በተከናወነው ክትትል በሕገወጥ የውጭ ምንዛሪ ላይ ተሳታፊ የነበሩ 48 ግለሰቦችና ከፍተኛ መጠን ያላቸው የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች እንዲሁም ከድርጊቱ ጋር የተያያዙ የባንክ ደብተሮችና ልዩ ልዩ ሰነዶች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ መደረጉ ተገልጿል፡፡
በቁጥጥር ስር የዋሉት ግለሰቦች የውጭ ሀገር የምንዛሪ ዋጋን የሚተምኑ፣ የሚሰበስቡና ሰብሳቢዎችንም የሚያሰማሩ መሆናቸው በመግለጫው ተጠቁሟል፡፡
ሕገወጥ ድርጊታቸውንም ሕጋዊ ፈቃድ ባላቸው የተለያዩ የንግድ ድርጅቶች ፣የችርቻሮ ሱቆች፣ቡቲኮች፣ ግሮሰሪዎችና ሱፐርማርኬቶች ሽፋን እንደሚያከናውኑ፤ በተሽከርካሪዎች ላይም ጭምር ይፈጽሙ እንደነበር አመላክቷል፡፡
በሕገ ወጥ መንገድ የሚሰበሰበው የውጭ ምንዛሪ በወንጀል የተገኘን ገንዘብ ከሀገር ለማሸሽ እንዲሁም የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሪ አቅም በማሳጠት ከፍተኛ የሆነ የዋጋ ግሽበት በማስከተል ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ለመፍጠር ታቅዶ ሲከናወን እንደነበር በጥናት መለየቱ ተገልጿል፡፡
በወንጀል ድርጊቱ ተጠርጥረው ከተያዙት ውስጥም ለህወሓት ድጋፍ ከሚያደርጉ የሽብር ቡድኑ ደጋፊዎች ጋር በትስስር የሚሠሩና ቀደም ብሎም የውጭ ምንዛሪን በሕገወጥ መንገድ ወደ ትግራይ ሲያስገቡ የነበሩ ይገኙበታል ነው የተባለው፡፡
ይህም በተቀናጀ መልኩ በውጭም በሀገር ውስጥም ሀብት ለማሸሽና የውጭ ምንዛሪ አቅምን ለማዳከም ይሠራ እንደነበር ያሳያል ብሏል መግለጫው፡፡
ሕገወጥ የውጭ ሀገራት ገንዘብ ዝውውሩ ወንጀል ከኢትዮጵያ እስከ ሶማሌ ላንድ ሀርጌሳ፣ ከዱባይና አሜሪካ እንዲሁም በሌሎች ሀገራትም ጭምር በፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ቤተሰባዊ በሆነ ኔትዎርክ ጭምር የተደራጀና የሚታዘዝ መሆኑም ተመላክቷል፡፡
በቁጥጥር ስር ከዋሉት ሕገወጥ የውጭ ምንዛሪ አስተላላፊዎቹ መካከል አንዳንዶቹ ከዚህ ቀደም በቁጥጥር ስር ውለው ፍርዳቸውን ጨርሰው የተለቀቁ ሲሆን÷ ከእዚህ በተጨማሪም ከ100 ሺ ህ ብር በላይ በማስከፈል ወደ ውጭ እንልካለን በማለት የዜጎችን ሀብትና ንብረት ሲዘርፉ የነበሩም በሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ወንጀልና በውጭ ምንዛሪ ዝውውሩ በነበራቸው ተሳትፎ እንዲያዙ ተደርጓል፡፡
አገልግሎቱ መንግሥት ሕገወጥ ድርጊቱን ለመከላከል የውጭ ሀገራት ገንዘቦች ከኢትዮጵያ የሚወጡባቸውን መንገዶችና ስልቶች በመረጃ በመለየትና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ጥብቅ ቁጥጥር ማድረጉንና በወንጀለኞች ላይ እርምጃ መውሰዱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡
የሀገርን ሀብትና ንብረት ዘርፈው ገንዘቡን በውጭ ምንዛሪ በማሸሽ ከሚፈጠሩ ኢኮኖሚያዊ ጫናዎች ሀገሪቷን ለመታደግ የሚደረጉ ጥረቶችንም በከፍተኛ ትኩረት እየተከታተለና አስፈላጊውን የማስተካከያ እርምጃዎች እየወሰደ መሆኑንም አመልክቷል፡፡
ኅብረተሰቡ ሕገወጦች በቁጥጥር ሰር እንዲውሉ ጥቆማ በመስጠት ላበረከተው አስተዋጽኦ ምስጋና ያቀረበው አገልግሎቱ ÷በቀጣይም ከደኅንነትና ከጸጥታ ተቋማት ጎን በመሆን የወትሮ ድጋፉን እንዲያጠናክር ጥሪ አቅርቧል፡፡