ሩሲያ በ52 ከፍተኛ የአየርላንድ ባለስልጣናት ላይ ማዕቀብ ጣለች
አዲስ አበባ፣ ሕዳር 7፣2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ሩሲያ በ52 ከፍተኛ የአየርላንድ ባለስልጣናት ላይ ማዕቀብ መጣሏን አስታውቃለች፡፡
የሀገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉዳዩን አስመልክቶ በሰጠው መግለጫ ÷ማዕቀቡ የተጣለው የአየርላንድ መንግስት እና ባለስልጣናቱ በሚያራምዱት ፀረ-ሩሲያ አቋም ምክንያት መሆኑን አስታውቋል፡፡
አየርላንድ በሩሲያ ላይ የምታሰራጨው ሀሰተኛ ፕሮፖጋንዳም የሀገራቱን የሁለትዮሽ ግንኙነት በእጅጉ እንደሚያሻክረው አንስቷል፡፡
ሞስኮ በአውሮፓ ህብረት እና በተለያዩ ተቋማት በሚደረጉ ስብሰባዎች ላይ መሰረተ ቢስ የሆነ ፀረ-ሩሲያ አቋም ያራምዳሉ ባለቻቸው የአየርላንድ ከፍተኛ ባለስልጣናትን ወደ ሀገሯ እንዳይገቡ ማዕቀብ ጥላለች፡፡
ማዕቀብ ከተጣላባቸው ከፍተኛ ባለስልጣናት ውስጥ የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ፣ መከላከያ ሚኒስትር፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚገኙበት አር ቲ ዘግቧል፡፡