በመዲናዋ ለቀጣይ ሶሰት ወራት የሚቆይ የፅዳት ንቅናቄ ተጀመረ

By Mekoya Hailemariam

November 26, 2022

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በአዲስ አበባ “ከተማዬን አፀዳለሁ፤ ፅዳትን ባህል አደርጋለሁ” በሚል መሪ ቃል ለቀጣይ 3 ወራት የሚቆይ  የፅዳት ንቅናቄ ማስጀመሪያ መርሐ ግብር ተካሄደ።

በምክትል ከንቲባ ማእረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ጥራቱ በየነ ንቅናቄውን ባስጀመሩበት ወቅት እንደተናገሩት፥ ፅዳት የከተማው ባህል ሆኖ እንዲዘልቅ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በእኩል ሃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል።

የከተማውን ፅዳት በግድየለሽነት በሚያቆሽሹ ግለሰቦች ፣ ድርጅቶችና ተቋማት ላይ ህግና ደንብን መሠረት ያደረገ የተጠናከረ እርምጃ እንደሚወሰድም አስታውቀዋል።

አቶ ጥራቱ በየነ አክለውም፥ የከተማው ፅዳትና ውበት መጠበቅ የሚጠቅመው ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል እንደመሆኑ አካባቢያቸውን በሚያቆሸሹ ጥቂት አካለት ላይ አስፈላጊው ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ ህብረተሰቡ ትብብር እንዲያደርግም መጠየቃቸውን ከከንቲባ ፅህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።