ኢትዮጵያ በአፍሪካ ደረጃ እየተካሄዱ ባሉ ኢኮኖሚያዊ ስብሰባዎች ላይ እየተሳተፈች ነው
አዲስ አበባ፣ ሕዳር 23፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ በ7ኛው የአፍሪካ የኢኮኖሚ ቀጠናዎች ድርጅት ዓመታዊ ስብሰባ እና በአፍሪካ ኅብረት 5ኛ ልዩ የኢኮኖሚ ሲምፖዚየም ላይ በናይጄሪያ አቡጃ አየተሳተፈች ነው፡፡
በሲምፖዚየሙ የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን በማፋጠን ፣ የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት እና የአረንጓዴ ልማት ፖሊሲ ማሻሻያዎችን በማጎልበት ረገድ ኢኮኖሚያዊ ቀጠናዎቹ የሚወጡት ሚና ተመላክቷል፡፡
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ዳንኤል ተሬሳ ÷ ኢትዮጵያ በኢንዱስትሪው ልማት ዘርፍ ያስመዘገበችውን ውጤት ፣ ቀጠናዊ አስተዋፅዖ እና የፖሊሲ ለውጥ አስረድተዋል፡፡
በተለይም ኢትዮጵያ በሥራ ዕድል ፈጠራ ፣በወጪ ንግድ ዕድገት እንዲሁም በክኅሎት እና በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ ያላትን ልምድ እና ቀጣናዊ ትሥሥር አካፍለዋል።