የሀገር ውስጥ ዜና

በኦሮሚያ ክልል ቆላማ አካባቢዎች ለሚተገበሩ ፕሮጀክቶች የ14 ሚሊየን ዶላር የዕርዳታ ስምምነት ተፈረመ

By Feven Bishaw

December 06, 2022

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 27፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ)በቦረና ዞንና በኦሮሚያ ክልል ቆላማ አካባቢዎች ለሚተገበሩ ፕሮጀክቶች የ14 ሚሊየን ዶላር የዕርዳታ ስምምነት ተፈረመ፡፡

ስምምነቱ የተፈረመው በገንዘብ ሚኒስቴርና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል መሆኑ ተገልጿል፡፡

ገንዘቡ በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአካባቢ ልማት፣ ሥርዓተ ፆታን ያገናዘበ የተቀናጀ ዘላቂ የውሃ ልማት፣ የአካባቢና የግል ንጽህና አገልግሎትን ለማስፋፋት ይውላልም ነው የተባለው፡፡

በውሃ አጠር አከባቢዎች ለሚኖሩ አርብቶ አደሮች የከርሰ-ምድር ውሃ ተደራሽ የሚሆንበት ፕሮጀክት እንደሚተገበርም ነው የተነገረው፡፡

በተጨማሪም የገንዘብ ድጋፉ በጤና፣ በማኅበራዊ ኑሮ፣ በሥነ-ምግብ እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራትን ለመደገፍ እንደሚውል ተገልጿል፡፡

የዕርዳታ ስምምነቱን የፈረሙት የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ሰመሪታ ሰውሰው እና የአፍሪካ ልማት ባንክ የምሥራቅ አፍሪካ ቀጠና ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አብዱል ካማራ መሆናቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡