የሀገር ውስጥ ዜና

በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የምሁራን የውይይት መድረኮች እየተካሔዱ ነው

By ዮሐንስ ደርበው

January 02, 2023

አዲስ አበባ፣ ታኅሣሥ 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በሰመራ፣ ወልድያ ፣ ጋምቤላ እና እንጂባራ ዩኒቨርሲቲዎች “በሀገር ግንባታ የምሁራን ሚና ምን መሆን አለበት?” በሚል ርዕሰ ጉዳይ የምሁራን ውይይት እየተካሔደ ነው፡፡

የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እና የሰመራ ዩኒቨርሲቲ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ስለሽ ግርማ÷ በመድረኩ የውይይት መነሻ ሐሳብ አቅርበዋል፡፡

በዚህም አባቶቻችን በጠላቶቻችን ላይ ድል ቢያደርጉም ለምን በዕድገት መድገም አልቻልንም? የሚለውን መመርመር እንደሚያስፈልግ አንስተዋል፡፡

በሀገር ግንባታ የምሁራን ሚና ምን መሆን አለበት? እንደ ሀገር የተገኙ ለውጦችንና እያጋጠሙ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት የምሁራን ውይይት አስፈላጊ መሆኑን አመላክተዋል፡፡

የኢትዮጵያን የዕድገት ጉዞ ለማፋጠን የምሁራን ከፍተኛ ተሳታፊነት አስፈላጊ ነው የተባለ ሲሆን÷የምሁራን የምክክር መድረኩም እስከ ታኅሣሥ 26 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ እንደሚቀጥል ተመላክቷል፡፡

በተመሳሳይ የወልድያ ዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ካውንስል “በሀገር ግንባታ የምሁራን ሚና” በሚል ርዕሰ ጉዳይ ዛሬ ውይይት መካሔድ ተጀምሯል፡፡

የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታና የወልድያ ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ነመራ ገበየሁ÷ የውይይቱ ዓላማ ምሁራን በሀገር ግንባታ ሊኖራቸው በሚገባ አዎንታዊ ሚና ላይ ያተኮረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

እንዲሁም በሐረማያ፣ ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ፣ ሐዋሳ፣ ዋቸሞ፣ ደብረ ማርቆስ፣ ጎንደር፣ ሚዛን ቴፒ፣ ቡሌሆራ፣ጋምቤላና እንጂባራ ዩኒቨርሲቲዎች “የምሁራን ሚና በሀገር ግንባታ” በሚል ርዕስ ውይይት እየተካሔደ መሆኑን ከዩኒቨርሲቲዎቹ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!