የፓን አፍሪካኒዝም ሻምፒዮን የተማሪዎች የእግር ኳስ ውድድር ተጀመረ
አዲስ አበባ፣ ታኅሣሥ 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) 2ኛው የፓን አፍሪካኒዝም ሻምፒዮን የተማሪዎች የእግር ኳስ ውድድር በአዳማ ከተማ ተጀምሯል፡፡
በማስጀመሪያ መርሃግብሩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ዋና ፀሃፊ ባህሩ ጥላሁን ÷ የፓን አፍሪካኒዝም ሻምፒዮን ውድድር ተተኪ ስፖርተኞችን ከማፍራት አንፃር ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ጠቁመዋል፡፡
የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዲኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት በበኩላቸው÷መሰል ውድድሮች ተተኪ ስፖርትኞችን ከማፍራት ባሻገር ክልሎች እርስ በእርሳቸው ግንኙነታቸውን የሚያጠናክሩበት መድረክ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
በውድድሩ ስድስት የወንድና አራት የሴት የእግር ኳስ ቡድኖች ተሳታፊ ሲሆኑ÷ ውድድሩን በድል የሚያጠናቅቁ ቡድኖች ለ2ኛ ጊዜ በታንዛኒያ በሚካሄደው የፓን አፍሪካ ሻምፒዮን ተሳታፊ እንደሚሆኑ ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
ውድድሩ ለተከታታይ ሶስት ቀናት እንደሚቆይም ተገልጿል፡፡
በሰላማዊት ተስፋየ