በአርቲስት ማሪቱ ለገሠ ስም ጎዳና ተሰየመ
አዲስ አበባ፣ ታኅሣሥ 30፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር በክብር ዶክተር አርቲስት ማሪቱ ለገሠ ስም ጎዳና ሰየመ፡፡
የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት መረጃ እንዳመላከተው÷ በኮምቦልቻ ከተማ ውስጥ የተገነባው አዲሱ የአውሮፕላን ማረፊያ (ኤርፖርት) መንገድ “የክብር ዶክተር አርቲሰት ማሪቱ ለገሠ” ጎዳና ተብሎ ተሰይሟል፡፡
አርቲስት ማሪቱ ለገሠ ከ22 ዓመታት የአሜሪካ ቆይታ በኋላ ታኅሣሥ 24 ቀን 2015 ዓ.ም ወደ ሀገሯ መመለሷ ይታወሳል፡፡
በዛሬው ዕለት ደግሞ የደሴ ከተማ አስተዳደር የክብር ዶክተር አርቲስት ማሪቱ ለገሠን በክብር አቀባበል አድርጎላታል፡፡
በደሴ ከተማ በተደረገላት ደማቅ አቀባበል ላይ የደሴ ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሳሙኤል ሞላልኝ÷ “በደሴ ከተማ በቅርቡ በምንገነባው የባህል ማዕከል ውስጥ አዳራሹን በክብር ዶክተር ማሪቱ ለገሠ ስም ሰይመናል” ብለዋል ሲል አሚኮ ዘግቧል፡፡