ቻይና በታይዋን አቅራቢያ ተጨማሪ ወታደራዊ ልምምድ አካሄደች
አዲስ አበባ፣ ጥር 1፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ቻይና ወታደራዊ ልምምዶችን በታይዋን አቅራቢያ ማካሄዷን አስታውቃለች፡፡
ቤጂንግ ከአንድ ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ የአሁኑን ጨምሮ ሁለት ወታደራዊ ልምምዶችን በታይዋን አቅራቢያ ማካሄዷ ተገልጿል፡፡
ልምምዶቹ የሀገሪቷን የዓየር ፣ የምድር እና የባሕር ኃይሎች ብቃት ለመፈተሽ የተካሄዱ መሆናቸውን የቻይና ምሥራቃዊ ዕዝ ጦር ቃል አቀባይ ኮሎኔል ሺ ዪ ገልጸዋል፡፡
አያይዘውም ጥምር ልምምዶቹ ሌሎች የውጭ ኃይሎችና የታይዋን ተገንጣዮች ለሚቃጡት ግጭት ቀስቃሽ እርምጃ የማስጠንቀቂያ መልዕክት ለማስተላለፍ ያለመ መሆኑን አመላክተዋል፡፡
የታይዋን ፕሬዚዳንት ጽኅፈት ቤት በበኩሉ÷ ድርጊቱን መሰረተ ቢስ ውንጀላ ሲል ማጣጣሉን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡