ዓለምአቀፋዊ ዜና

የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት የዓለምን የኢኮኖሚ ዕድገት ተጽዕኖ ውስጥ ከትቶታል – አይ ኤም ኤፍ

By Mikias Ayele

January 21, 2023

አዲስ አበባ፣ ጥር 12፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት የዓለምን የኢኮኖሚ ዕድገት ተጽዕኖ ውስጥ እንዲገባ ማድረጉን የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይ ኤም ኤፍ) ገለጸ፡፡

የአይ ኤም ኤፍ ዳይሬክተር ክሪስታሊና ጆርጂያቫ  በዓለም አቀፉ ኢኮኖሚ ፎረም ላይ ባደረጉት ቆይታ÷ በጦርነቱ  ለመከላከያና ለጦር መሣሪያዎች የሚውለው ገንዘብ የዓለምን የኢኮኖሚ ዕድገት ሊያሳድግ የሚችል እንደነበር አንስተዋል፡፡

በሞስኮ እና ኪዬቭ መካከል እየተካሄደ ያለው ጦርነት ዓለም አቀፋዊ መሆኑን እና የኔቶ አባል ሀገራትን ጨምሮ ሌሎች ሀያላን ሀገራት የጦር መሳሪያ በማቅረብ መሳተፋቸውን ጠቁመዋል፡፡

ውጤቱም በዓለም ላይ የበለጠ ድህነት እና ረሃብ እንዲከሰት ማድረጉን የገለፁት ዳይሬክተሯ ÷ የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት ከዓለም  የኢኮኖሚ እድገት ጋር የሚደረግ ጦርነት መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡

ቡልጋሪያዊዋ የምጣኔ ሃብት ምሁር አክለውም እየተካሄደ ያለው ግጭት ለበለጸገው የዓለም ክፍል ሳይቀር ስጋት መሆኑን ጠቁመው÷ በተለይም አውሮፓ የጦርነቱ ተፅዕኖ ገፈት ቀማሽ ልትሆን እንደምትችል አመላክተዋል፡፡

የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት ከጊዜ ወደ ጊዜ የዓለም የምግብ ቀውስን እያባባሰ መምጣቱን ሩሲያን ታይምስ ዘግቧል፡፡