ዓለም አቀፉ ግብረ ሠናይ ድርጅት በኢትዮጵያ እና ኡጋንዳ ለሚገኙ ሴት ተፈናቃዮች የሚውል የ1 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ አገኘ
አዲስ አበባ ፣ ጥር 24 ፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) “አክሲየን” የተሰኘ ዓለም አቀፍ ግብረ-ሠናይ ድርጅት በኢትዮጵያ እና ኡጋንዳ ለሚገኙ ሴት ሥደተኞች ድጋፍ የሚያውለው 1 ሚሊየን ዶላር ከኮናርድ ሂልተን ፋውንዴሽን ማግኘቱን አስታወቀ፡፡
ግብረ-ሠናይ ድርጅቱ ÷ ሥደተኞቹ በሚገኙበት ሀገር ከሚሠሩ የፋይናንስ ፣ የንግድ እና የማኅበረሰብ ተቋማት ጋር በመተባበር ሥራ መጀመር የሚያስችላቸውን መነሻ ገንዘብ እና ሥልጠና እንደሚያመቻች ዛሬ በገፁ ባወጣው መረጃ አመላክቷል፡፡
በኢትዮጵያ እና በኡጋንዳ ገጠራማ የሀገራቱ ክፍሎች ከመሠረታዊ አገልግሎቶች የተገለሉ ከ 2 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ሥደተኞች መሥፈራቸውንም ነው የጠቆመው፡፡
የአሲየን ግብረ-ሠናይ ድርጅት ፕሬዚዳንት እና ዋና ሥራ አሥፈፃሚ ሚካዔል ሽላይን ÷ ሴት ሥደተኞቹ የፋይናንስ አቅርቦት እንዲያገኙ ከሂልተን ፋውንዴሽን ጋር በመተባበር እንሠራለን ብለዋል፡፡
በሚኖሩበት ማኅበረ-ሰብ ውስጥ በአነስተኛ ንግዶች ላይ ተሠማርተው በኢኮኖሚ ጠንካራ የሚሆኑበት መንገድ እንዲፈጠር እና ከራሳቸው አልፈው አካባቢያቸውን በኢኮኖሚ እንዲገነቡ ብድር እንደሚያቀርቡም ተመልክቷል፡፡